Tuesday, December 18, 2012

አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ



አባታችን አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሚያዚያ 8 ቀን ተጸንሶ ታህሳስ 9 ቀን ተወለደ፡፡

ኢትዩጵያዊው ጻድቅ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስኢትዮጵያዊው አባት አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባቱ መልዓከ ምክሩ እናቱ ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡የተወለደበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ይባላል፡፡በዚያች ሀገር እግዚአብሔርን የሚፈራ ስሙ መልዓከ ምክሩ የሚባል ደግ ሰው ባለቤቱም ወለተ ማርያም ሁለቱም ደጋጎች እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው በእግዚአብሔር ህግ ጸንተው የሚኖሩ መልካም ስራን በመስራት እንደ ዘካርያስና ኤልሳጴጥ እውነተኞች ነበሩ፡፡ሁለት ደጋጎች ልጆችም አሏቸው የተባረከ መልካም ፍሬን የሚያፈራ በመጾም በመጸለይ እግዚአብሔርን የሚ
ያገለግል በጸሎቱ ሰውን የሚጠቅም በጻድቃንም ዘንድ የተመረጠ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ዘወትር ወደ እግዚአብሔር እና ወደ ድንግል ማርያም ይለምኑ ነበር፡፡
ነብየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ጆሮውን ወደ ልመናቸው አዘነበለ እንዳለ መዝ 3329 እግዚአብሔር አምላክ በዓይነ ምህረት ተመለከታቸው ልመናቸውንም ሰምቶ አባታችን አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሚያዚያ 8 ቀን ተጸንሶ ታህሳስ 9 ቀን ተወለደ፡፡በተወለደ እለትም ተነስቶ በእግሩ ቆሞ 3 ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብሎ ጣዕም ባለው አንደበቱ ተናገረ፡፡9 ጊዜም ህጻናትን ለሚያናግሩ ገዥ ለሚሆኑ ለአጋይዝተ አለም ስላሴና ለእመቤታችን ለመስቀሉም ሰገደ፡፡እዚያ ተሰብስበው የነበሩ ብዙ ሰዎች ከህጻኑ አንደበት የስላሴን ምስጋና ሰምተው ፈጽመው አደነቁ ዳግመኛም በዚህ ህጻን ላይ የእግዚአብሔር ጸጋ አድሮበታል ብለው እየተጨዋወቱ ወደ ሀገራቸው ገቡ፡፡
አባቱና እናቱም መጀመሪያ ስለመወለዱ ዳግመኛም የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስን ምስጋና በማቅረቡ ደስ አላቸውና እግዚአብሔር ይህን ህፃን ሰጠን እኛ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስዕል ፊትና ለፍጥረት ሁሉ ለምትራራ ከሁሉ በላይ በሆነች አምላክን በወለደች በቅድስት ድንግል ማርያም ስዕል ፊት ቁመን እንደለመንን ልመናችንን ሰምታ የተመረጠ ልጅ ሰጠችን ብለው አመሰገኑ፡፡የመንጻት ወራት በተፈጸመ ጊዜ 40 ቀን አባትና እናቱ በጸራ ወርቅና ብር ንጉስ ይኩኖ አምላክ ወደ አሰራው እግዚአብሔር አብ ቤተክርስቲያን ወስደው አዳም 40 ቀኑ ወደ ገነት እንደገባ በቤተክርስቲያን ስርዓት ተጠመቀ፡፡ አዳም በአርባ ሄዋን በሰማንያ ቀን ወደ ገነት እንደገቡ ኩፋሌ 49 ካህናትም መንፈስ ቅዱስ እንዳናገራቸው ስሙን እስትንፋሰ ክርስቶስ ብለው ሰየሙት ስጋ ወደሙን ተቀብሎ ወደ ቤቱ ተመለሰ የስሙም ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቀው አደገ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቦናውን ብሩህ አድርጎለት 5 ዓመቱ የቅዱሳን መጽሐፍትን፣ ቃላትን ፣ብሉያትንና ፣ሐዲሳትንም፣ድርሳናትንም አወቀ፡፡ ከመምህር ኪራኮስ የመፅሐፍትን ትምህርት ከነትርጓሜው 7 ዓመቱ ጨረሰ፡፡ በማስተዋል ሲመለከት አባቱንና እናቱን ዘመዶቹን የተወ ቃሌን ይጠብቃል መንግስተ ሰማያትን ይወርሳል ይህን ያላደረገ ሊያገለግለኝ አይችልም የሚለውን አገኘ ማቴ 1037 ይህንንም ቃል በልቦናው ይዞ የምነናውን ስርዓት ይጠብቅ ነበር፡፡ 7 ጊዜ በመዓልት 7 ጊዜ በሌሊት በየዕለቱ 150 መዝሙረ ዳዊትን ሲያደርስ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ፊቱን በትምህርተ መስቀል አማትቦ ጸሎት በጀመረ ጊዜ እጆቹን ሲዘረጋ ወጥመዳቸውን ያጠመዱ አጋንንት በነፋስ ፊት እንዳለ ጢስ ተነው ይጠፋሉ እየተሯሯጡም ፈጥነው ይሸሻሉ፡፡
ከዚህ በኃላ ስሙ ማርቆስ ከሚባል ጳጳስ ድቁናን ተቀበለ፡፡ ልጄ ለእግዚአብሔር ትገዛ ዘንድ ወደ ገዳም ብትሄድ ሰውነትህን ለመከራ አዘጋጅ እንዳለ ሲራክ 21 ይህንን አለም ናቀ፡፡ ልዩ ክብር የሚሆን የምንኩስናን ልብስ ይቀበል ዘንድ በተወለደ 14 ዓመቱ ወደ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደ ከባህር ዳር ቆሞ የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ያለመርከብ ባህሩን ተሻግሮ ወደ ቤተክርስቲያን ገባ፡፡የኢየሱስ ሞዐ ልጅ የሚሆን አበምኔቱ በመነኮሳት መጽሐፍ እንደተፃፈ 3 ዓመት ፈተነው፡፡ በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኮሳት ምግብ ሊሆናቸው ከባህር ውስጥ አሳን በማውጣት ያገለግል ነበር፡፡ከአባ ህንጻ ደብረ ድባ ከሚባል ቦታ የቅስና ስልጣን ተቀበለ፡፡

አባታችን አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ለማስተማር ወደ አባቶቹ ሀገር ወደ አባቱ መቃብር በገባ ጊዜ እዚያው ደርሶ ቤተክርስቲያን ሰራ እለቱን ስንዴ ዘርቶ፣ወይን ተክሎ፣ጽድንም ወይራን ግራርን ተክሎ በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት እለቱን አድርሷል፤ስንዴውን ለመስዋዕት ወይኑን ለቁርባን በታምራት አድርሷል፡፡ከእለታት በአንድ ቀን አባታችን በጸሎት ላይ ሳለ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ከብሩህ ደመና ጋር ወደ እርሱ መጥቶ በደመና ጭኖ ከፈጣሪው ዘንድ አደረሰው፡፡ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በቅዱሳኖቹ እንዲባረክ ካደረገ በኃላ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልን አዘዘው ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ አድርሰህ አሳየው አለው፡፡መላዕኩም እንደታዘዘው አደረገ፡፡መልሶም ወደ ኢትዮጵያ ምድር ደብረ ዛብሒል ወደ ምትባል ቦታ አደረሰው፡፡ ከዚያም ደርሶ ድንቅ ታምራትን አደረገ ውሃም ከአለት ላይ እያመነጨ ህሙማንን ፈወሳቸው፡፡
በባህር ውስጥ ጠልቆ ዘወትር በሄደበት ሀገር ሀሉ ሲጸልይ የሚያርፍበትን ቦታና ስጋዬ የሚቀበርበትን ቦታ ግለጽልኝ ብሎ በጸለየ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ተልኮ መጥቶ የአባትህ አባት ከሸዋ ሀገር መጥቶ ታቦተ እግዚአብሔር አብን ወደ አስተከለበት ወደ አባ ሙሴ ደብር ወደ አባትህና እናትህ ቦታ ዳውንት ምትባል ሀገር ሂድ ብሎ የእረፍት ቦታውን ነገረው፡፡ከዚያም ወደ ብዙ ገዳማት በመሄድ ቡራኬን ተቀበለ፡፡ ከአራት ዓመት በኃላ አረጋውያን መነኮሳትን ተሰናበታቸው መርቀውት ተለያዩ፡፡ የኢትዮጵያን ገዳማት ተዘዋውሮ እየጎበኘ ጎዣም ደረሰ ፤በዚያ እያስተማረ፣ እያጠመቀ የታመሙትን እየፈወሰ፣የእውራንን አይን እያበራና ሙታንን እያስነሳ በዚያ ተቀመጠ፡፡በባህር ውስጥም ገብቶ 9 ዓመት ለኢትዮጵያ ጸለየ፡፡
ከዘጠኝ ዓመት በኃላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ መጥቶ ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ ይህችን ሀገር እና የኢትዮጵያን ህዝቦች ምሬልሃለሁ ከዚህች ባህር ውጣ አለው፡፡ አባታችንም ከባህር ውስጥ ወጥቶ ተንበርክኮ ለጌታችን ሰገደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የማረፊያህ ቦታ ምስራቅ ወደ ምትሆን ወደ ዳውንት ሂድ ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ አባታችንም በአስራ ሰባት ዓመቱ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄድበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ደረሰች፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ጸለየ አለቀሰ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁን ቀጥ ብለሽ ቁሚ አላት ጸሐይም ወደ ኃላ ተመልሳ በአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቃል ቆመች ደብረ አሰጋጅ እንደገባ ጸሐይም አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ አለችው እግዚአብሔር ይፍታሽ ባላት ጊዜ ገባች፡፡
እድሜው ሰላሳ ሦስት በሆነ ጊዜ ወደ ደብረ ድባው አበምኔት መጥቶ ሚያዝያ ዘጠኝ ቀን ምንኩስናን ተቀበለ፡፡በዚያ ደንጋይ ፈልፍሎ ዋሻ አዘጋጀ፡፡ ሉቃስ የሳላት ከግብፅ የመጣች የድንግል ማርያምን ስዕል አስገብቶ የዋሻውን በር ዘጋ፡፡ ያለ ደቀመዝሙሩ ልብሰ ክርስቶስ በስተቀር ከሌላ ሰው ጋር አይገናኝም፡፡በዚህ ድንቅ ድንቅ ታምራትን እያደረገ ሁለት መቶ አርባ ነፍሳትን ከሲኦል አወጣ፡፡

1 comment:

  1. ye Abatachin Abune Estinfase Kristos Bereketu, Miljaw ayleyen

    ReplyDelete