Monday, December 30, 2013

ታህሳስ 22


ታህሳስ 22 በቤተክርስቲያን አስተምህሮ ብስራተ ገብርኤል ይባላል፤ ይህም ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን ጌታን እንደምትወልድ ብስራቱን የነገረበት ቀን ነው፤ እንዴት ብስራቱንማ የነገራት መጋቢት 29 ቀን ካሉ ትክክል ነው፤ ብስራቱን የነገራት መጋቢት 29 ቀን በዕለተ እሁድ ከቀኑ ሦስት ሰዓት ላይ ነው፡ ታዲያ ዛሬ ለምን እናከብረዋለን ካሉ ምክንያቱ እንዲህ ነው፤ ምንግዜም ወርሃ መጋቢት ታላቁ ዓቢይ ጾም የሚውልበት ወር ነው በዚህ በዓቢይ ጾም ደግሞ ሐዘን፤ ለቅሶ፤ ጾም፤ ጸሎት እንጂ ደስታ፤ ፌሽታ እልልታ፤ ጭብጨባ የለም ፍጹም የሐዘን ወራት ነው ፍትሃ ነገስት አንድምታ አንቀጽ 15 ፤ ታዲያ ቅዱሳን አባቶቻችን እንደዚህ ዓይነት ስርዓት ሰሩ የመጋቢት 27 ስቅለቱን ጥቅምት 27 ቀን እንዲሁም የመጋቢት 5 አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ እረፍት ቀን ወደ ጥቅምት 5 ቀን ዞሮ እንዲከበር አደረጉ፡፡ የመጋቢት 29 ብስራቱን ደግሞ ታህሳስ 22 ቀን ዞሮ እንዲከበር ያደረገው ታላቁ አባት የጥልጥልያ ኤጲስ ቆጶስ ደቅስዮስ ይባላል በእመቤታች ፍቅር ልቡ የነደደ ታላቅ ጻድቅ ነው የእመቤታችንን ታአምራቷን የሚናገር መጽሐፍ የሰበሰበ አባት ነው፡፡ የጌታን ልደት ከመከበሩ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ብስራቱ መከበር አለበት ብሎ ስርዓት ሰራ አገሬውንም ሰብስቦ ታላቅ የደስታ በዓል አደረገ እመቤታችን ተገለጸችለት ወዳጄ ደቅስዮስ ባንተ ደስ አለኝ እንዳከበርከኝ እኔም አከብርሃለው አለችው ሰማያዊ ልብስና ሰማያዊ ወንበር ሰጠችው ይህችን ልብስ ካንተ ሌላ ማንም አይለብሳትም ይህችንም ወንበር ካንተ ሌላ ማንም አይቀመጥባትም አለችው፡ የዚህ ታላቅ አባት እረፍቱ ታህሳስ 22 በዛሬዋ ቀን ነው፡ ከእርሱ በኃላ ሌላ ኤጲስ ቆጶስ ተሾመ ልብሱን እለብሳለው በወንበሩም እቀመጣለው አለ ተው ይቅርብህ እመቤታችን እንዲህ ብላ ተናግራለች ይሉታል እርሱም ሰው እኔም ሰው እርሱም ኤጲስ ቆጶስ እኔም ኤጲስ ቆጶስ ብሎ በትዕቢት ልብሱን ለበሰው በወንበሩም ተቀመጠ ክፉኛ አወዳደቅ ወደቀ ደቅስዮስ ሰርቶልን ያለፈውን ስርዓት ቤተክርስቲያን ተቀብላ ይኸው ዛሬም ድረስ ታከብረዋለች በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ ብስራተ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ታቦተ ህጉ ወጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል፡፡ ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፡፡

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

Friday, December 27, 2013

ታህሳስ 19


እንኩዋን ለታላቁ መልአክ ለቅዱስ ገብርኤል አመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ:: ታህሳስ 19 በዚህች ቀን… ንጉሡ ናቡከደነፆር የወርቁን ምስል አሠራ፤ በባቢሎንም አውራጃ በዱራ ሜዳ አቆመው ። ለወርቁ ምስል ሁሉም እንዲሰግድ እንዲንበረከክ አዘዘ ሁሉም ሰገደ ተንበረከከ ከእነዚህ ሦስት የልዑል እግዚያብሔር ብላቴናዎች በቀር ስማቸው ሲድራቅ ሚሳቅና አብደናጎም ይባላል፤ ናቡከደነፆርም በብስጭትና በቍጣ ሦስቱን ብላቴናዎች ያመጧቸው ዘንድ አዘዘ ወደ ንጉሡ ፊት አመጡአቸው። አምላኬን አለማምለካችሁ፥ ላቆምሁትም ለወርቁ ምስል አለመስገዳችሁ እውነት ነውን? እንግዲውስ በሚነድድ እሳት እቶን ውስጥ ትጣላላችሁ፤ ከእጄ የሚያድናችሁ አምላክ ማን ነው? ብሎ ተናገራቸው። ሲድራቅና ሚሳቅ አብደናጎም እንዲህ ሲሉ መለሱለት ንጉስ ሆይ፥ በዚህ ነገር እንመልስልህ ዘንድ አስፈላጊያችን አይደለም የምናመልከው አምላካችን ከሚነድደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ደግሞም ያድነናል! ነገር ግን፥ ንጉሥ ሆይ፥ እርሱ ባያድነን እንኳን አማልክትህን እንደናመልክ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንደማንሰግድ እወቅ አሉት። የዚያን ጊዜም ናቡከደነፆር በሲድራቅና በሚሳቅ በአብደናጎም ላይ ቍጣ ሞላበት፥ የፊቱም መልክ ተለወጠባቸው፤ እርሱም ተናገረ፥ የእቶንም እሳት ይነድድ ከነበረው ይልቅ ሰባት እጥፍ አድርገው እንዲያነድዱት እና እሳቱ ይጥሉአቸው ዘንድ አዘዘ፤ የዚያን ጊዜም እነዚህ ብላቴናዎች ከነልብሳቸው ከነመጐናጸፊያቸው ታስረው እሳት ውስጥ ተጣሉ። ናቡከደነፆር አሟሟታቸውን ሊመለከት ቆመ ወደ እሳቱም ተመለከተ አራት ሰዎችም በእሳት ውስጥ ሲመላለሱ አየ ተደነቀ ፈጥኖም ተነሣ፤ አማካሪዎቹንም። ሦስት ሰዎች አስረን በእሳት ውስጥ ጥለን አልነበረምን? ብሎ ተናገራቸው። እነርሱም። ንጉሥ ሆይ፥ እውነት ነው ብለው መለሱለት።እርሱም። እነሆ፥ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎች አያለሁ፤ ምንም አላቈሰላቸውም፤ የአራተኛውም መልክ የአማልክትን ልጅ ይመስላል ብሎ መለሰ። ይህም ታላቁ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡ ናቡከደነፆር ድምጹን ከፍ አድርጎ ከእሳቱ እንዲወጡ ተጣራ የራሳቸው ጸጉር አልተቃጠለም ልብሳቸውም እንዲሁ ናቡከደነፆር ከዚህ በኃላ እንዲህ ሲል እግዚያብሔርን አመሰገነ “በእርሱ የታመኑትን ባሪያዎቹን ያዳነ፥ የሲድራቅና የሚሳቅ የአብደናጎም አምላክ ይባረክ” ትንቢተ ዳንኤል 3፡ 1- 30 ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፡፡ 
 

Sunday, December 15, 2013

ታህሳስ 6


 በዚህች ቀን ታላቋ ሰማዕት የቅድስት አርሴማ ዓመታዊ በዓሏ ነው፤ ይህም ቅዳሴ ቤቷ የተከበረበት ነው ...በዚህም ቀን ታላላቅ ተአምራቶች ተደርገዋል፤ በተለይም ይህ ቀን በአገረ አርማንያ ልዩ ስፍራ አለው፤ በመዲናችን አዲስ አበባ አስኮ ቃሎ ተራራ ላይ ግሩም ቤተክርስቲያን አላት ታዋቂው ገዳሟ ግን ወሎ ሲሪንቃ ይገኛል። መስከረም 29 በሰማዕትነት ያረፈችበት ነው፤ እነዚህን ሁለቱን ቀናት ቤተክርስቲያን በደማቁ ታከብራቸዋለች፤ሌላው በዛሬው ቀን ታላቁ አባት አብርሃም ሶርያዊው ያረፈበት ቀን ነው፤ ይህ አባት ተራራን ያፈለሰ ነው፤ ታሪኩ ወዲህ ነው አባ አብርሃም የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ በነበረበት ወራት አንድ አይሁዳዊ ወደ ንጉሱ ገብቶ እንዲህ ይለዋል “እነዚህ ክርስቲያኖች የሚገርሙ ናቸው በወንጌላቸው ላይ የሰናፍጭ ቅንጣት እምነት ካላችሁ ይህንን ተራራ ተነቅለህ ወደዚያ ሂድ ብትሉት ይሆንላቹዋል ይላል፤” ይህ የሐሰት ወንጌል ነው፤ከመካከላቸው ይህን የሚያደርግ አንድስ እንኳን የለም ይለዋል” ንጉሱም አባ አብርሃምን አስጠርቶ “በእርግጥ ወንጌላችሁ እንዲህ ይላልን ?” ይለዋል አዋን ንጉስ ሆይ ብሎ ይመልስለታል፤ ታዲያ የክርስቲያኖች ሁሉ አባታቸው አለቃቸው አንተ ነህ እስኪ አድርግና አሳየኝ ይለዋል፤ እሺ ግን 3 ቀን ብቻ ይስጡኝ ብሎ ወጣ፤ ጨነቀው ወደ እምቤታችን ቤተክርስቲያን ገብቶ 3 ቀን 3 ሌሊት እህል ሳይበላ ውኃ ሳይጠጣ አለቀሰ፤ እመቤቴ አታሳፍሪኝ አላት፤ ተገለጸችለት ይህ ላንተ አይሆንም ግን ወደ ከተማ ውጣ በእንስራ ውሃ ተሸክሞ የሚሄድ ሰው ታገኛለህ፤ ስሙ ስምዖን ጫማ ሰፊ ነው፤ አንድ አይና ነው፤ አንዱን አይኑን ያጠፋው የልጄን ትዕዛዝ ለማክበር ብሎ ነው፤ ለእርሱ ይቻለዋል እርሱ የሚልህን አድርግ ትለዋለች፤ እንደተባለውም ስምዖንን ያገኘዋል፤ ነገሩን ሁሉ ይገልጽለታል፤ እሺ ለማንም ስሜንም ስራዬንም እንዳትገልጽቢኝ፤ ህዝቡን ሰብስብ እኔ በተሰወረ ቦታ ሆኜ የማሳይህን እየተመለከትክ አድርግ አንተ የምታደርገውን ደግሞ ህዝቡ ያድርግ አለው፤ ንጉሱም ሰራዊቱም ህዝቡም ይህንን ታአምር ለማየት ተሰበሰበ፤ 41 ጊዜ ኪራላይሶን ብለው ሶስት ጊዜ ሰገዱ፤ ከዚያም አባ አብርሃ ስምዖን የሚያሳየውን እየተከተለ መስቀሉን አውጥቶ ወደ ተራራው አማተበ፤ ተራራው ወደ ላይ ተነሰ፤ ታላቅ ፍርሃት ሆነ፤ ሶስት ጊዜ ተራራው ወደ ላይ እየተነሳ ይቀመጣል በተራራው ስር ከወዲያ ማዶና ከወዲህ ያሉ ሰዎች ይተያዩ ነበር ይላይ፤ ንጉሱም ህዝቡም እጹብ እጹብ አሉ ምስጉን እግዚያብሔርንም አመሰገኑ፤ ንጉሱ ክርስቲያን ሆኖ ተጠምቋል ብዙ አብያተክርስቲያናትንም አንጿል። አባ እብርሃምም ተፈርቶና ተከብሮ በቅድስናም ኖሮ በዛሬዋ እለት አርፏል። ከቅድስት አርሴማ፤ ከአባ አብርሃምና ከስምዖን ጫማ ሰፊ በረከታቸውን ያድለን። አሜን

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

ታህሳስ 5

በዚህች ቀን ቅድስት አውጋንያ አረፈች፤ አገሯ እስክንድርያ ነው አባቷ አገር ገዢ ነበር ፊሊጶስ ይባላል ጣኦት አምላኪ ነው እናቷ ግን ደግ ክርስቲያን ነበረች በድብቅ ክርስትናን አስተማረቻት ስታድግ ታላላቅ መኳንንቶች አጯት እርሷ ግን ጠፍታ ወደ አባ ቴዎድሮስ ገዳም ገባች መነኮሰች ማንም ሰው እንዳያውቃት ፍጹም ወንድ መሰለች ስሟንም አባ አውጋንዮስ አሰኘች፤ አባቷ ጠፍታ መቅረቷን ባወቀ ጊዜ መሪር ለቅሶ አለቀሰ እሷን የሚመስል ጣኦት አስቀርጾ ማምለክ ጀመረ። ከአንድ ዓመት በኃላ ትጋቷን አይተው መነኮሳቱ የገዳሙ አበምኔት አድርገው ሾሟት፤ (አበምኔት ለወንድ እንደሆነ ልብ ይሏል) እግዚያብሔር በሰይጣናትና በድውያን ላይ ፍጹም ስልጣን ሰጣት ከብዙ አገር በሽተኞች እየመጡ በእጇ ይፈወሱ ነበር፤ ከእለታት አንደ ቀን ግን እንዲህ ሆነ አንዲት ሴት ቅድስት አውጋንያን ባየቻት ጊዜ ወንድ መስላት ፍጹም ወደደቻት፤ ምንኩስናህን ትተህ ባል ሆነከኝ ከኔ ጋር ኑር አለቻት፤ ሂድ አንተ ሰይጣን ብላ አባረረቻት፤ ባሳፈረቻት ጊዜ ወደ አገር ገዢው ሄዳ በዚያ ገዳም የሚኖር መነኩሴ ሊደፍረኝ ሲል አምልጬ መጣሁኝ አለችው፤ ዘፍጥረት 39 14 መኮንኑ በሰማ ጊዜ ተቆጣ ሁሉንም መነኮሳት ታስረው እንዲሰቃዩም አደረገ፤ የሞቱም አሉ፤ ቅድስት አውጋንያ ስቃያቸውን ባየች ጊዜ መኮንኑን ጌታዬ እውነቱን እነግርሃለው የምፈልገውን ነገር ግን አትከልክለኝ አለችው፤ አስማለችውም፤ ከዚያም ልጁ አውጋንያ እንደሆነች ገለጸችለት፤ አንገቷን አቅፎ አለቀሰ፤ እኔም ባንቺ አምላክ አምናለው አላት ከነቤተሰቦቹም ተጠመቀ የበቃ ታላቅ አባት እስከመሆን ደርሶ በሰማእትነት ነው የሞተው እርሷም ወደ ሮም ሄዳ የገዳም እመምኔት ሆና ለብዙ ዘመናት ለረጅም ወራት በተጋድሎ ኖራ ታህሳስ በባተ በአምስተኛው ቀን አረፈች፤ በረከቷ ይደርብን ከጻድቁ አቡዬ በረከታቸውንም ያሳትፈን።
LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

Friday, December 13, 2013

ታህሳስ 4

 
በዚህች ቀን የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስ ወንድም የተመሰገነ ቅዱስ እንድርያስ በሰማዕትነት አረፈ፤ የዚህ ሐዋርያ ቁጥሩ ከ 12ቱ ሐዋርያት ነው፤ ማቴ 4፤ 18 ቀድሞ በገሊላ ባህር ማዶ በቤተሳይዳ ዓሳ አጥማጅ ነበር፤ ሰውን ታጠምዳለህ ብሎ ጌታ ጠራው ተከተለው። ዓለምን ዞረው ለማስተማር ዕጣ ሲያወጡ ለቅዱስ እንድርያስ ልዳ ደረሰችው ልዳ ማለት የቅዱስ ጊዮርጊስ አገር ናት፤ ሊያስተምር ወደዚያች አገር ገባ፤ ጣኦት አምላኪዎች ወሬውን ሰምተው ሊጣሉት ሾተል ይዘው ወጡ፤ ሐዋርያው እንድርያስ ግን ከፍ ካለ ቦታ ላይ ቆሞ እንዲህ ሲል ሰበከ " የአህዛብ ጣኦታት የሰው እጅ ስራ ናቸው ዓይን አላቸው አያዩም፤ ...ጆሮ አላቸው አይሰሙም፤ አፍንጫ አላቸው አያሸቱም፤ እጅ አላቸው አይዳስሱም፤ እግር አላቸው አይሄዱም በጉሮሮአቸውም አይናገሩም የሚሰሯቸው የሚያምኑባቸው ሁሉ እንደ እነርሱ ይሆናሉ፤ መዳን በእግዚያብሔር ነው እርሱም እየሱስ ክርስቶስ ነው እያለ ሰበከ” ከቃሉ ጣዕም ከአንደበቱን ቅልጥፍና ከነገሩ ማማር የተነሳ የወገባቸው ትጥቅ ተፈታ ሾተላቸውን ጣሉ፤ በጌታችን አምነው ተጠመቁ ይላል። ይህ ሐዋርያ በሰው ቋንቋ የምትናገር የምትላላከው እርግብ ነበረች፤ ተረፈ ኤርሚያስ 10፤24 ዘፍጥረት 8፤ 8 በነዚህ ጥቅሶች ኖህ ከርግብ ባሮክ ከንስር ጋር በሰው ቋንቋ ሲነጋገሩ ሲላላኳቸውም እናያለን፤ ሐዋርያው እንድርያስ ከእርግብ ጋር ሲነጋገር ህዝቡ ይገረም ነበር። ይህ ሐዋርያ በዛሬዋ እለት ግብራቸው እጅግ ወደ ከፋ አገረ ሰዎች ገብቶ ሲያስተምር አሰቃይተው ገድለውታል። በረከቱ ይደርብን

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

Monday, December 9, 2013

ታህሳስ 1


እነሆ የተባረከ የታህሳስ ወር ባተ፤ ይህ ወር ቀኑ 9 ሰዓት ነው ሌሊቱ 15 ሰዓት፤ ቀኑ በጣም አጭር ነው ቶሎ ይመሻል ሌሊቱ በጣም ረጅም ነው፤ ታህሳስ 1 በዚህች ቀን በገለዓድ ይኖር የነበረው ቴስብያዊው ኤልያስ የተወለደበት ቀን ነው፤ ታሪኩ 1ኛ ነገስት 17፤1 ላይ በስፋት ይገኛል፤ በእሳት ሰረገላ የተሰወረው ጥር 6 ቀን ነው፤ እነዚህን ሁለት ቀናት ቤተክርስቲያን ነብዩን አስባ ትውላለች፤ ይህ ነብይ በአገራችን በስሙ የታነጹለት አብያተክርስቲያናት አሉት ከነዚህም በመዲናችን አዲስ አበባ ርዕሰ አድባራት እንጦጦ ደብረ ሐይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን የሚገኘው ቤተክርስቲያን አንዱ ነው፤ ኤርትራ ውስጥም አንድ ቤተክርስቲያን አለው፤ ዛሬ በደማቁ ተከብሮ ይውላል፡፡ አክአብና ኤልዛቤል ምሰኪኑን ናቡቴ ከአባቶቹ እርስት አፈናቅለው በግፍ በገደሉት ጊዜ፤ ንጉሱን ሳይፈራና ሳያፍር በግልጽ የዘለፈ ነብይ ነው፤ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይንም የለጎመ ነው ይህንንም ያዕቆብ በመልእክቱ እንዲህ ሲል መስክሯል ያዕ 5 ፤ 16 "የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች። ኤልያስ እንደ እኛ የሆነ ሰው ነበረ፥ ዝናብም እንዳይዘንብ አጥብቆ ጸለየ፥ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር አልዘነበም፤ ሁለተኛም ጸለየ፥ ሰማዩም ዝናብን ሰጠ ምድሪቱም ፍሬዋን አበቀለች"
ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፡፡

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

Friday, December 6, 2013

ህዳር 29


በዚህች ቀን ተፍጻሚ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አረፈ። በዚህች ሴት ታሪክ እንደርደር ሳራ ትባላለች አገሯ አንጾኪያ ነው ደግ ክርስቲያን ነች ጣኦት አምልኮ በተስፋፋበት ወራት ሁለት ልጆች ወልዳ ነበር የክርስትና ጥምቀትን ልታስጠምቃቸው ግን አልቻለችም ምነው ቢባል ካህንም ቤተክርስቲያንም ከዚያች አገር ተሰደው ነበርና፤ እስክንድርያ ወስጄ ላስጠምቃቸው ብላ መርከብ ተሳፍራ ጉዞ ጀመረች፤ ታላቅ ሞገድ ተነሳ መርከቧ ልትገለበጥ ደረሰች በዚህ ጊዜ ልጆቼ ሳይጠመቁ ሊሞቱ ነው ብላ ፈራች፤ምላጭ አውጥታ ጡቷን ሰነጠቀች በደሟም የልጆቿ ግንባር ላይ መስቀል እየሰራች በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ብላ አጠመቀቻቸው፤ወዲ...ያውኑ ወጀቡ ማዕበሉ ጸጥ አለ እስክንድርያ በሰላም ደረሱ ወደ ሊቀ ጳጳሱ ገባች የዚህ አባት ስም ተፍጻሜ ሰማዕት ጴጥሮስ ይባላል፤ ልጆቿን ሊያጠምቅ ወደ ጸበሉ ሲጠጋ ጸበሉ እንደ ሰም ይረጋል፤ ሌሎች ህጻናት ሲመጡ መፍሰስ ይጀምራል ለሁለተኛ ጊዜ ልጆቿ ሲመጡ ጸበሉ እንደ ሰም ይረጋል ሶስት ጊዜ እንዲሁ ሆነ ነገሩ ምንድን ነው ብሎ ጠየቃት የሆነውን ሁሉ ነገረችው፤ በጣም ተደነቀ እግዚያብሔርንም አመሰገነ ይላል። ተፍጻሜ ሰማዕት ጴጥሮስ 3 ደቀ መዛሙርት ነበሩት አርዮስ፤አኪላስና እለእስክንድሮስ ይባላሉ፤ ለአርዮስ ክህነት ሰጥቶ የሾመው ይህ አባት ነው፤ ምን ዋጋ አለው አርዮስ አጥብቆ ተመራመረ ወልድ ፍጡር ነው ብሎ ወደቀ፤ ይህንንም በድብቅ ለሰው ማስተማር ጀመረ፤ በዚህ ጊዜ ጌታችን ለተፍጻሚተ ሰማዕት ጴጥሮስ የተቀደደ ልብስ ለብሶ ተገለጸለት አንተ ማን ነህ ይለዋል የናዝሪቱ እየሱስ ነኝ ታዲያ ልብስህ ለምን ተቀደደ ይለዋል “አርዮስ ሰጠጣ ለልብስየ” ይለዋል አርዮስ ልብሴን ቀደደው ማለት ነው፤ ከባህሪ አባቴ ከአብ ከባህሪ ህይወቴ ከመንፈስ ቅዱስ ለይቶ ፍጡር ነው አለኝ ይለዋል፤ ይህን ራዕይ እይቶ ብዙም ሳይቆይ አርዮስ መጣ ቁጭ አድርጎ መከረው “በልብህ ያለውን ኑፋቄ ካሰብክ እንዳትናገር ከተናገርክ እንዳትደግመው ብሎም ያስጠነቅቀዋል፤ ሊሰማው ግን አልቻለም፤ አውግዞ ይለየዋል፤ ጓደኞች አኪላስና እለእስክንድሮስ ሊማልዱለት ይመጣሉ፤ አባታችን አርዮስ ተመልሻለው እያለ ነው ከግዝቱ ፍታው ይሉታል፤ እርሱም እንደማይመለስ ጌታ በራዕይ ነግሮኛል አሁን እኔ የምሞትበት ጊዜ ደርሷል ከኔ በኃላ አኪላዎስ ሊቀ ጳጳስ ትሆናለህ ጓደኝነት በልጦብህ አርዮስን ከግዝቱ ትፈታዋለህ ነገር ግን ብዙ አትቆይም ትሞታለህ ብሎ ትንቢት ይነግራቸዋል፤ የእረፍቱ ቀን እንደደረሰም አውቆ “ጌታ ሆይ የኔን ሞት የሰማእታት መጨረሻ አድርግሊኝ ከኔ በኃላ የእንድስ እንኳን ሰማእት ደም እይፍሰስ” ብሎ ጸለየ፤ህዳር 29 ቀን የዲዮቅልጥያኖስ ጭፍሮች አንገቱን ቆርጠው ገድለውታል፤ለዚህም ነው ቤተክርሰቲያን “ተፍጻሚ ሰማዕት ጴጥሮስ” ብላ የምትጠራው የሰማእታት መጨረሻ ማለት ነው፤ ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከአባታችን በረከት ያሳትፈን። 

ህዳር 27

በዚህች ቀን ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት አረፈ፤ አገሩ ፋርስ ነው የንጉስ ወታደር ሲሆን ቀድሞ የሚያመልከው ጸሐይና ጨረቃን ነበር፤ በኃላ ጌታችን ጠራው ፍቅሩንም በልቡ ቀረጸበት ጣኦት ማምለኩን ተወ፤ በዚህም ንጉሱ ተቆጣ ደሙ እንደ ውሃ እስኪወርድ አስገረፈው፤ የሚገርመው እንደ ግንድ ድቡልቡል እስኪሆን ድረስ አካሉን ትንሽ ትንሽ እየቆረጡ ጨረሱት በመጨረሻም አንገቱን ቆርጠው ገደሉት፤ የዚህ አባት መቃብሩ ግብጽ ብሕንሳ ይገኛል፤ ብሕንሳ ማለት የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የትውልድ ስፍራ ናት። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ :- አርዮስን ለማውገዝ ኒቂያ ከተሰበሰቡት 318ቱ ሊቃውንት መካከል በአርዮሳውያ...ን እንዲሁም በጣኦት አምላኪዎች መከራ ያልደረሰበት ያልተሰቃየ አባት የለም፤ ከሁሉም የሚገርመው ግን የቶማስ ነው፤ መርዓስ የምትባል አገር ኤጲስ ቆጶስ ነው፤ ጣኦት አምላኪዎች ይህን አባት ለ 22 ዓመት አካሉን ትንሽ ትንሽ እየቆረጡ ወስደው ለጣኦታቸው ያጥኑት ነበር፤ ከጥፍሮቹ ጀምረው፤ ጣቶቹን፤ እጆቹን፤ ጆሮዎቹን፤ ከንፈሩን ምላሱን አፍንጫውን... ቆርጠው ጨረሱት በግንድ የተለበለበ ግንድ መሰለ ይላል፤ ነፍሱ ግን አልወጣችም ደቀ መዛሙርቱ በቅርጫት ተሸክመው በኒቂያ ከጉባዬው አስገቡት፤ ንጉስ ቆስጠንጢኖስ ጉባዬውን ለማስጀመር ወደ አዳራሽ ሲገባ መጀመሪያ አቅፎ የሳመው ይህንን አባት ነው፤ አገላብጦ ሳመው ይላል፤ ይህ አባት እንዲህም ሆኖ በርካታ አሰደናቂ ተአምራቶች ይሰራ ነበር። ታሪካቸው ስለሚመሳሰል በጥቂቱ አነሳነው እንጂ ሰፊ ታሪክ አለው፤ በረከታቸውን ያድለን።

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

Tuesday, December 3, 2013

ህዳር 26


ህዳር 26 ገድለኛው አባ እየሱስ ሞአ አረፉ። የተወለዱት ጎንደር ጎርጎራ ልዩ ስሙ ዳህና ሚካኤል በ 1196 ዓ/ም ነው፤ በ 30 ዓመታቸው መንነው ደብረ ዳሞ ሄዱ በአባ ዮሐኒ እጅ መነኮሱ በተጋድሎም ኖሩ፤ ከዚያም ቅዱስ ገብርኤል እየመራቸው ሐይቅ እስጢፋኖስ መጡ፤ ሐይቅ እስጢፋኖስ ማለት ከደሴ 30 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኝ ሲሆን የመሰረቱት ካልዕ ሰላማ የተባሉ ግብጻዊ ጻድቅ ናቸው፤ ገዳሙን ከሰሩ በኃላ የማንን ታቦት እናስገባ ብለው ሲያስቡ ቶራ የምትባል እንስሳ ጭነት ተጭና ከመካከላቸው ተገኘች፤ ጭነቱን አውርደው ቢያዩት በሐር ጨርቅ የተጠቀለለ ሁለት ታቦት አገኙ አንዱ የእስጢፋኖስ አንዱ የጊዮርጊስ " ይህንን ታቦት በእ...የሩሳሌም የሚኖሩ የተሰወሩ ቅዱሳን ከእግዚያብሔር ታዘው የላኩት ነው" የሚል ጽሑፍም አገኙ ይላል። ይህ ከሆነ ከ 400 ዘመን በኃላ ነው አባ እየሱስ ሞኣ ወደዚህ ቦታ የመጡት ለ 52 ዓመት ቀን ቀን መንፈሳዊ ስራቸውን ይሰራሉ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ቆመው ሲጸልዩ ያድራሉ፤ በእንዲህ ያለ ፍጹም ተጋድሎ ኖረው ህዳር 26 በዛሬዋ ቀን አርፈዋል፤ በነገራችን ላይ ተክልዬን ያመነኮሱ አባት ናቸው። እንደዚህ ነው የመነኮሳት አባት እንጦንስ ነው እንጦንስ መቃርስን ወለደ መቃርስ ጳኩሚስን ጳኩሚስ አቡነ አረጋዊን አቡነ አረጋዊ አባ ዮሐኒን አባ ዮሐኒ የሐይቁን አባ እየሱስ ሞአን ወለዱ አባ እየሱስ ሞኣ ደግሞ ተክልዬን ወለዱ። በዚህ ገዳም የሚከበሩ በዓላት መስከረም 15 የእስጢፋኖስ ፍልሰተ አጽሙ፤ ህዳር 26 የአባታችን እረፍት እንዲሁም ጥር 1 የእስጢፋኖስ እረፍቱ ናቸው፤ በእውነቱ የሚገርም ገዳም ነው ገነት እንጂ ምድር አይመስልም። ቦታውን ለማየት ያብቃን የጻድቁ በረከትንም ያሳትፈን።

ህዳር 25


በዚህች ቀን ቅዱስ መርቆሪዎስ በሰማዕትነት አረፈ፤ አገሩ ሮም ነው፤ በወጣትነቱ ከሃዲው ንጉስ ኡልያኖስ ላቆመው ጣኦት አልሰግድም ብሎ የሰው ልጅ ሊሸከመው የማይችለውን መከራ ተቀበለ፤በመጨረሻም ህዳር 25 በዛሬዋ ቀን አንገቱን ቆርጠው ገደሉት ደም ውኃና ወተት ከአንገቱ ፈሰሰ። ይህ ሰማዕት በአገራችን በስሙ በርካታ ገዳማትና አብያተክርስቲያናት አሉት በተለይም ቅዱስ ላሊበላ ካነጻቸው 11 ውቅር አብያተክርስቲያናት አንዱን ቤተ መርቆሪዎስ ብሎ ሰይሞለታል፤ በዚህ በሰሜን ሸዋ ደግሞ የሚገርም ገዳም አለው፤ ካህናት በማህሌት ወረብ ሲያቀርቡ ስዕሉ ያሸበሽባል ይዘላል፤ ይህንንም አይቶ ማረጋገጥ ይቻላል፤ በመዲናችን አዲስ አበባ ቅዱስ ኡራኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ታቦቱ አለ ዛሬ በደማቁ ተከብሮ ይውላል። መርቆሪዎስ ከሞተ በኃላ ፈረሱ ለሰባት ዓመት ወንጌልን አስተምሯል፤በኃላም አንገቱን ቆርጠው ገድለውታል እንዴት ብሎ የሚገረም የበልአምን አህያ ይጠይቃት፤ እኛስ እስመ አልቦ ነገር ዘይሳኣኖ ለእግዚያብሔር ብለን እንመልሳለን፤ ዘኁልቁ 22፤28 ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አለ ቃል የሌለው አህያ በሰው ቃል ተናግሮ የነብዩን እብድነት አገደ ይላል 2ጴጥ 2፤16። ከሰማዕቱ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

ኀዳር 24



ኀዳር 24 በዚች ዕለት . . .
1. ካህናት ሰማይ ሱራፌል የድርሻችንን እንወጣ፣ ከበረከቱ ተካፈሉ
ሱራፌል ማለት አጥንተ መንበሩ ለልዑል ማለት ነው : : በቁጥር ሃያ አራት ናቸው: : መንበሩን እያጠኑ ቅዱስቅዱስ ቅዱስ እያሉ ያለ እረፍት ያመሰግናሉ
2. አባታችን ተክለሃይማኖት በሐይቅ እስጢፋኖስ የአቡነ ኢየሱስ ሞዓ ረድዕ ሆነው እያገለገሉ እያለ ተመጥቀው ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር ሆነውየሥላሴን መንበር ያጠኑበት ቀን: ጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ እንደ አንዱ ሁነው መንበረ ጸባዎትን ያጠኑበት ታላቅ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም በፍቅር እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን የጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት እረድሄት በረከታቸው ምልጃና ጸሎታቸው ከመላው ህዝበ ክርስቲያን ጋር ይሁን አሜን።
3. በዚህች ቀን የጎሬው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሚካኤል አረፉ፤ ትውልዳቸው ጎንደር ነው 1887 ዓ/ም ትምህርታቸው ወሎ ቦሩ ሜዳ፤ በ 1921 ዓ/ም እንዲህ ሆነ እንዲህም ተደረገ፤ አራት አባቶች ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ግብጽ ይላካሉ ጵጵስና ለመቀበል፤ ከነዚህ አራት አባቶች መካከል አንዱ አቡነ ሚካኤል ነበሩ፤ ግብጽ ለረጅም ዓመት ዝናብ ጠፍቶ ምድሪቱ ነዳ ነበረ፤እነዚህ አባቶች የግብጽን መሬት ሲረግጡ ወዲያውኑ ደመና ግጥም አለ በዚያው ቀንም ዝናብ ዘነበ ይላል፤ ብጹዕ አቡነ ሚካኤል ከግብጽ ከተመለሱ በኃላ የጎሬ ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመደቡ ለ 8 ዓመትም ህዝቡን በፍቅር አገለገሉ፤ በ 1929 ዓ/ም ጣሊያን ገባ ጎሬንም ያዘ በወቅቱ የነበሩት አገር ገዢ ቢተወድድ ወልደ ጻድቅና ሹማምንቶቻቸው ወደ ከፋ ሲሰደዱ አቡነ ሚካኤል ህዝቡን ለተኩላ ትቼ አልሄድም ብለው እዚያው ቀሩ ለህዝቡ ስለ አገር ፍቅር ስለ ወገን ክብር ስለ ነጻነት መስበክ ጀመሩ፤ የፋሺሽት ጦር መሪ ኮሎኔል ማልታ ወታደሮቹን ልኮ አቡኑን አስያዛቸው፤ እንዲህም አላቸው “ ለጣሊያን ለመገዛት ቃል ይግቡ ህዝቡንም ያሳምኑልንና እንለቆታለን” አላቸው፤ “እኔ ግን እልሃለው” አሉት አቡኑ፤ “እኔ ግን እልሃለው ለናንት የሚገዛ አይደለም ህዝቡ መድሪቱ የተወገዘች ትሁን” አሉት በድፍረት፤ ተቆጣ ጉድጓድ አስቆፈረ፤ ጉድጓዱ አጠገብ አቡኑን አቆመ አልሞ ተኳሾችንም አዘጋጀ፤ “ጥቂት ጸሎት ላድርግ ፍቀዱሊኝ” አሉ አቡነ ሚካኤል፤ፈቀዱላቸው ጸሎት አደረጉ መስቀላቸውን አውጥተው ግንባራቸው ላይ አስጠጉ፤ “አሁን የፈለጋችሁትን ማድረግ ትችላላችሁ” አሉ፤ “ተኩስ” የሚል ትእዛዝ ተሰማ፤ ነፍሰ ጋዳዮቹ በተኩስ እሩምታ የአቡኑን ደረትና ግንባር በሳሱት፤ ወደቁ ወደ ጉድጓዱም ተወረወሩ አፈርም ለበሱ፤ከዚህ በኃላ ኮሎኔል ማልታ ሽማግሌዎችን ሰብስቦ እኛ አቡኑን ለምነናቸው ነበር እርሳቸው እምቢ ብለው ነው በአመጽ ስራ በመገኘታቸው ነው፤ እናንተስ ምን ትላላችሁ የአቡኑ መገደል ትክክል ነበር ወይንስ አልነበረም ብሎ አፋጠጣቸው፤ ሽማግሌዎቹ ትክክል አልነበረም ለማለት ፈሩ፤ ከመካከላቸው አንድ የንግግር ዘይቤ አዋቂ አለቃ ቢረሳው የተባሉ አዛውንት ሽማግሌዎቹን ወክለው ለመናገር ቆሙ፤ እንዲህም አሉ “እናንተም ደግ ገደላችሁ፤ እርሳቸውም ደግ ሞቱ ብለው ተናገሩ፤” ቅኔ መሆኑም አይደል “ ደግ ” የሚለው ወርቁ ነው አቡነ ሚካኤል ህዝብ የሚወዳቸው በጣም ደግ ነበሩ። 1936 ዓ/ም የሰማእቱ አጽም ተለቅሞ ጎሬ ደብረ ገነት ማርያም ቤተክርስቲያን በክብር ተቀምጧል፤ የሚያሳዝነው ግን አቡነ ሚካኤልን ጣሊያን ከገደላቸው እኛ የገደልናቸው ይበልጣል፤ በአገራችን ለቁጥር የሚበዙ ሀውልቶች አደባባዮች እውራ ጎዳናዎች የተለያየ ስያሜ ተሰጥቷቸዋል ደጎል አደባባይ ፑሽኪን አደባባይ ቸርቸል ጎዳና…ወዘተ እነዚህ ሰዎች እኮ ለራሳቸው ኖረው ለራሳቸው የሞቱ ግለሰቦች ናቸው፤ ሰማእቱ ግን ውድ ህይወታቸውን ለአገር ለወገን ለነጻነት የሰው ናቸው፤ የረባ መታሰቢያ እንኳን የላቸውም፤ ዝክራቸው ቀርቷል ስማቸውም ተረስቷል፤ “ አገሬ ኢትዮጰያ ሞኝ ነሽ ተላላ የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ” ያለው ማን ነበር ? ህዳር 22 ለኤች አይቪ ኤድስ ሻማ በርቶለታል፤ግጥም መወድስ ዝማሬም ቀርቦለታል፤ሐመ ከመ ዮም “እንደዛሬው ለአመቱ ያድርሰን” ብለንም ተመራርቀንበታል፤ ይገርማል ህይወቱን የሰጠ ሕይወትን ከሚነጥቅ ሲያንስ ይገርማል፤ይደንቃል…፤ ከሰማእቱ አቡነ ሚካኤል፤ ከጻድቁ ተክልዬ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ በረከታቸውን ያድለን።

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

ህዳር 21







እናታችን ጽዮን

በዲ/ን ኅሩይ ባየ


በቅዱሳት መጻሕፍት ጽዮን የሚለው ቃል ተደጋግሞ በነቢያቱ ተነግሯል፡፡ ሆኖም የጽዮን ትርጉም እንደተነገረበት ዐውደ ትንቢት እንደተሰበከበት መዋዕለ ትምህርት ምስጢሩ ይለያያል፡፡

በዚህ ጽሑፍ በጥቂቱ የምንመለከተው ታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ እንዴት እንደመጣች፣ ኅዳር 21 ቀን ስለምናከብረው ዓመታዊ በዓል፣ በታቦተ ጽዮን እና በዘመነ ሐዲስ በተገለጠችው በእመቤታችን በቅድስትድንግል ማርያም ያለውን ምስጢራዊ ትርጉም ነው፡፡ታቦት አንቺ ነሽ» ብሏል፡፡ 

ታቦተ ጽዮን በፈቃደ እግዚአብሔር በነቢዩ ሙሴ አማካኝነት ለሰው ልጆች ተሰጥታ እስራኤላውያን ሲባረኩባት፣ መሥዋዕታቸውን ሲያቀርቡባት ከእግዚአብሔር ሲታረቁባት ኖረዋል፡፡ከአራት ሺሕ ሦስት መቶ ሃያ ሰባት ዓመተ ዓለም (4327 ዓ.ዓ.) ጀምሮ ለአርባ ዓመታት ያህል እስራኤላውያንን በክህነት ያገለግል የነበረው ካህኑ ዔሊ ዕድሜው ሲገፋ ሁለት ልጆቹን ጠርቶ ምሉዕና ዱግ /ዋናና ምክትል/ አድርጎ ሾማቸው፡፡

በደብተራ ኦሪት ታቦተ ጽዮንን እንዲያገለግሉ የተሾሙት ሁለቱ ወጣት ካህናት /አፍኒን እና ፊንሐስ/ ፈቃደ እግዚአብሔርን ተላልፈው ሦስት ታላላቅ በደሎችን ፈጸሙ፡፡ የመጀመሪያው በደል፤ በሙሴ ሥርዓት በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት በርታ በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት የምትጠፋ መብራት እንድትቀመጥ የተሠራ ሥርዓት ነበር፡፡ ሆኖም አገልግሎት ከሌለ ሲበራ ማደሩ ለምን ? ብለው መቅረዙን አነሡ፤ መብራቱንም አጠፉ፡፡ ሁለተኛ፣ ለራሳቸው ሥጋዊ ጥቅም ቅድሚያ ሰጥተው ለመሥዋዕት እንዲሆን ከመጣው እንስሳ ታርዶ ስቡ ሳይጤስ፣ደሙ ሳይፈስ ሥጋውን እየመረጡ ተመገቡ፡፡ሦስተኛ ጸሎት እናደርሳለን ሥርዓተ አምልኮ፣ እንፈጽማለን ብለው ወደ መገናኛው ድንኳን ይመጡ ከነበሩት እስራኤላውያን ቆነጃጅት ጋራ በዝሙት ወደቁ፡፡ አባታቸው ካህኑ ዔሊም የልጆቹን በደል እያየ እንዳላየ እየሰማ እንዳልሰማ ቸል በማለቱ እግዚአብሔርአዘነ፡፡ በዚህም ምክንያት ፍልስጥኤማውያንን አስነሥቶ በጦርነት ቀጣቸው፡፡

ዕብራውያን በጦርነት ውሎ ያለልማዳቸው በአሕዛብ ተሸነፉ፡፡ ሕዝበ እስራኤልም ግራ ቢገባቸው «ድል የተነሣነው ታቦተ ጽዮንን ይዘን ባለመዝመታችን ነው» ብለው አፍኒን እና ፊንሐስ ጽላቱን እንዲሸከሙ አድርገው ወደ ፍልስጥኤማውያን የጦር ምሽግ ገሠገሡ፡፡ ሆኖም ያሰቡት ሳይሳካ ታቦተ ጽዮን ተማረከች፣ አፍኒንና ፊንሐስ ሞቱ፤ ዕብራውያንም በጦርነቱ ድል ተደረጉ፡፡ፍልስጥኤማውያንም ታቦተ ጽዮንን ማርከው ዳጎን ከተባለው ጣዖታቸው ላይ አስቀመጧት፡፡ በማግስቱ ሲመለሱ ዳጎን ተገልብጦ ታቦተ ጽዮን በላይ ተቀምጣ አገኟት፡፡ በማግስቱም ተመሳሳይ ድርጊት ተፈጽሞ ዳጎን ወድቆና ተሰባብሮ አገኙት፡፡ 1ሳሙ 5÷4 ይኽን በተመለከተ ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጽጌ ድንግል ሰቆቃወ ድንግል በተባለው ድርሰቱ፤ 

«ታቦተ አምላከ እስራኤል ጽዮን ዘነገደት ምድረ ኢሎፍሊ፤ 

ወቀጥቀጠቶ ለዳጎን ነፍሳተ ብዙኃን ማህጎሊ፤ 

አመ ነገደት ቁስቋመ በኀይለ ወልዳ ከሃሊ፤ 

ወድቁ አማልክተ ግብፅ መናብርተ ሰይጣን ሐባሊ፡፡ 

ወተኀጉሉ ኲሎሙ ዘቦሙ አስጋሊ. . .፤ 

ወደ ኢሎፍሊ ምድር ተማርካ የሔደች የእስራኤል አምላክ የቃል ኪዳኑ ታቦተ ጽዮን የብዙዎችን ነፍሳት ያጠፋ ዳጎንን ሰባበረችው፡፡ ድንግል ማርያምም ሁሉን ማድረግ ከሚችለው ከልጇ ጋር ግብፅ ወደሚባል ሀገር በሔደች ጊዜ የሐሰተኛ ሰይጣን ዙፋኖች የሆኑ የግብፅ ጣዖታት ፈረሱ ጠንቋይ አስጠንቋይ ያላቸው ሁሉ ዐፈሩ» በማለት በንጽጽር አስቀምጦታል፡፡ ኢሳ 19÷1 ኃይል እና ድል ማድረጉን በዳጎን የጀመረችው ታቦተ ጽዮን የፍልስጥኤማውያንን መንደር በአባርና በቸነፈር በእባጭም መታች፡፡ ሕዝበ ፍልስጥኤምም ታቦተ ጽዮን ወደ እስራኤል ምድር እንድትመለስ አደረጉ፡፡

በእንደዚህ ዓይነት ታላቅ ክብር በሀገረ እስራኤል ትኖር የነበረችው ታቦተ ጽዮን ወደ ሀገራችን ወደ ኢትዮጵያ መምጣቷ ታላቅ የሆነ መንፈሳዊ ሐሴት እንዲሰማን ያደርጋል፡፡

የታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት

ከአርባ ሁለት ጊዜ በላይ ስሟ ተደጋግሞ የተጠቀሰው ሀገር ቅድስት ኢትዮጵያ በእግዚአብሔርየተወደደች ለመሆኗ ነቢያቱ መስክረዋል፡፡ ከነቢያት አንዱ አሞፅም፤ «የእስራኤል ልጆች ሆይ ለእኔ እንደ ኢትዮጵያ ልጆች አይደላችሁምን ?» ብሎ እግዚአብሔር መናገሩን ጽፏል /9÷7/፡፡ ከሁሉም ከፍ ባለመልኩ ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት፤ «ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች» ብሎ ሕዝበ ኢትዮጵያ እደ ሕሊናውን እና እደ ልቡናውን ዘወትር በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ በጾምና በጸሎት፣ በምጽዋትና በትሩፋት፣ ዘርግቶ በሃይማኖት ጸንቶ፣ በምግባር ቀንቶ የሚኖር በመሆኑ፤ ሕዝቡ ሕዝበ እግዚአብሔር ምድሪቱ ሀገረ እግዚአብሔር ተብለዋል፤ /መዝ.68÷31/፡፡

ለታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ዋናው ምክንያት በእስራኤል እና በኢትዮጵያ መካከል የነበረው የሠመረ ግንኙነት ነው፡፡ ይኽም በመሆኑ የንግሥት ሳባ እና የንጉሥ ሰሎሞን ግንኙነት ሰፊውን ታሪክ ይዞ ይገኛል፡፡የንግሥተ ሳባ ዕቃ ግምጃ ቤት የነበረው ታምሪን ወደ ኢየሩሳሌም ሔዶ ንጉሥ ሰሎሞን ያሠራውን ቤተ መቅደስ ዓይቶ፣ የሰሎሞንን ጥበባዊ ዝና ሰምቶ በፍጹም መደነቅ ወደ ሀገሩ ተመለሰ፡፡ ያየውንና የሰማውን ለንግሥቲቱ አጫወታት፡፡ እሷም የሰማችውን ለማየት ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳ የሰሎሞንን መንፈሳዊና ሥጋዊ ጥበብ ተመልክታ እግዚብሔርን አመስግና ተመለሰች፡፡



ከንጉሥ ሰሎሞን ምኒልክን ፀንሳ ከኢየሩሳሌም ተነሥታ ባሕረ ኤርትራን ተሻግራ፣ ሐማሴን አውራጃ ስትደርስ አሥመራ ከተማ በሚገኘው ማይበላ ከተባለው ቦታ ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ የሕፃኑንም ስም የንጉሥ ልጅ ስትል «እብነ መለክ» አለችው፡፡ ይኽ ስም በዘመን ሒደት ምኒልክ ተብሎ ተለወጠ፡፡



ምኒልክ ተወልዶ በአእምሮ እያደገ ሲሔድ አባቴ ማን ነው ? አድራሻውስ ወዴት ነው ? እያለ ጥያቄ ቢያበዛባት በሃያ ሁለት ዓመቱ ወደ ኢየሩሳሌም ላከችው፡፡ ምኒልክም አባቱ ንጉሥ ሰሎሞንን አግኝቶ ሕገ ኦሪትንና የዕብራይስጥ ቋንቋ ሲያጠና ከቆየ በኋላ፤ ዐሥራ ሁለት ሺሕ እስራኤላውያንን አስከትሎ ከምድረ እስራኤል ወደ ኢትዮጵያ ጉዞውን አቀና፡፡



ከቀዳማዊ ምኒልክ ጋር ለጉዞ የተነሡ ዕብራውያን ከቤተሰቦቻቸው መለየታቸው ሳያሳዝናቸው ከታቦተ ጽዮን መለየታቸው እጅግ ከበዳቸው፡፡ ወዲያው በፈቃደ እግዚአብሔር ታቦተ ጽዮንን ከመንበሯ አንሥተው በሊቀ መላእክት በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ወደ ኢትዮጵያ ገቡ፡፡



ቀዳማዊ ምኒልክ እና እስራኤላውያን ታቦተ ጽዮንን ይዘው አክሱም የደረሱት ኅዳር 21 ቀን ነበር፡፡ ንግሥተ ሳባም የታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በጣም ስላስደሰታት በክብር ተቀበለቻቸው፡፡ «ወአንበርዋ ውስተ ሕፅነ ደብረ ሀገረ ማክዳ» እንዲል በአክሱም ከተማ መካከል ደብረ ማክዳ /ዛሬ ቤተ ጊዮርጊስ ከሚባለው/ ላይ ደብተራ ኦሪት ሠርተው አስቀመጧት፡፡



አሁን ያለው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በዘመናዊ ዐቅድ የታነፀው የአክሱም ጽዮን ገዳም ቅዳሴ ቤቱ ጥር 30 ቀን 1957 ዓ.ም ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ፣ ግርማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥ /የታላቋ ብሪታንያ ንግሥት/ እና ልዑል ፊልፕ ከክብር ባለሟሎቻቸው ጋር በተገኙበት ተከብሯል፡፡

ኅዳር ጽዮን በአክሱም

አክሱም ማርያም ጽዮን በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ መሠረታቸው ስትሆን ከተማዋም የኢትዮጵያ ሥልጣኔ መነሻ ናት፡፡ አክሱም በሕገ ልቡና የጸናች፣ ሕገ ኦሪትን የፈጸመች፣ በሕገ ወንጌል ያመነች ናት፡፡ ለዚህም ነው «ሕግ ይወጽእ እምጽዮን፤ ከጽዮን ሕግ ይወጣል» የሚለው ጥቅስ የሚነገረው፡፡

በዓለ ልደትን በላሊበላ፣ ጥምቀትን በጎንደር፣ ኅዳር ጽዮንን በአክሱም ጽዮን ሲያከብሩት ልዩ የሆነ ሥርዓት ስለሚቀርብባቸው ምእመናን መንፈሳዊ ደስታ ይሰማቸዋል፡፡

ኅዳር 21 ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል ነው ብለን በተለየ መልኩ የምናከብርበት ምክንያት፡- 

1. በብሉይ ኪዳን ታቦተ ጽዮን የፈጸመችውን ልዩ ልዩ ገቢረ ተአምራትን ለማሰብ

2. ቀዳማዊ ምኒልክ ከዐሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል የበኲር ልጆች ጋር ሊቀ ካህናቱን አዛርያስንና ታቦተ ጽዮንን ይዞ አክሱም የደረሰበት ዕለት በመሆኑ

3. በሦስት መቶ ሠላሳ ዓመተ ምሕረት በአብርሃ ወአጽብሃ ዘመነ መንግሥት ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ይሁን ተብሎ ዐዋጅ የታወጀበት

4. ዘካርያስ በተቅዋመ ወርቅ ምሳሌ ራእይ ያየበት

5. ነቢዩ ሕዝቅኤል በተቆለፈች ቤተ መቅደስ 

6. ዕዝራ በቅድስት ሀገር ምሳሌ ራእይ ያየበት

7. አብርሃና አጽብሃ በወርቅና በዕንቁ ያሠሩት ባለ አሥራ ሁለት ክፍል ቤተመቅደስ ለመጀመሪያ ጊዜ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረበት

8. በዘጠነኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዮዲት ጉዲት አብያተ ክርስቲያናትን ስታቃጥል ታቦተ ጸዮንን ይዘው ወደ ዝዋይ ሐይቅ ከተሰደዱ በኋላ ዘመነ ሰላም ሲጀመር አክሱም በነበሩ ካህናት አስታዋሽነት ከዝዋይ ወደ አክሱም የገባችበት ዕለት 

በመሆኑ በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ከፍ ባለ መንፈሳዊ በዓል እናከብራለን፡፡ ይኽ ሲባል ግን በዓሉ የሚከበረው በአክሱም ጽዮን ማርያም ብቻ ነው ማለት ሳይሆን፤ ታቦተ እግዝእትነ ማርያም ባለችበት ቦታ ሁሉ መከበሩን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ከዚሁ ጋርም የመመኪያችን ዘውድ፣ የመዳናችን ምክንያት፣ የንጽሕናችን መሠረት ስለሆነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያልተነበየ ነቢይ፣ ያልሰበከ ሐዋርያ፣ ያልተቀኘ ባለቅኔ ከቶ የለም፡፡ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወረደ፣ በቤዛነቱ ዓለምን አዳነ፣ ዳግመኛም በክበበ ትስብእት፣ በግርማ መለኮት ለፍርድ ይመለሳል ብንል ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሣው ሥጋ በመሆኑ ያለ ወላዲተ አምላክ ምስጢረ ሥጋዌን፣ ነገረ ድኅነትን፣ ነገረ ምጽአትን ማሰብ ከቶ የማይቻል ነው፡፡

«ዕግትዋ ለጽዮን፤ ጽዮንን ክበቧት» እንዳለ ነቢዩ፤ ዐሥርቱ ቃላት የተጻፈባትን የእስራኤል አምባና መጠጊያ የሆነችውን ታቦተ ጽዮንን ሌዋውያን ከበዋት ውዳሴ ያቀርቡላት እንደነበረው፤ ዛሬም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ካህናትና ምእመናን ከሩቅ እና ከቅርብ ተሰብስበው በማኅሌት፣ በዝማሬ፣ በቅዳሴና በውዳሴ ያከብሯታል፡፡

በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም እና በቃል ኪዳኑ ታቦት መካከል ጥልቅ የሆነ ምስጢራዊ ትምህርት አለ፡፡ /ዘፀ. 25÷9-20/፡፡ ይህቺ የቃል ኪዳን ታቦት በደብተራ ኦሪት በቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ የኖረች፣ የዮርዳኖስን ባሕር የከፈለች /ኢያ. 3÷14-17/፤ ቅጽረ ኢያሪኮን ያፈረሰች /ኢያ 6÷1-21/፤ ዳጎን የተባለ የፍልስጥኤማውያንን ጣዖት የቆራረጠች /1ሳሙ 5÷1-5/፤ በድፍረት ሊነካ የሞከረውን ኦዛን የቀሰፈች /1ሳሙ 6÷6/፤ በአቢዳራ ቤት ሦስት ወር ተቀምጣ ቤቱን በበረከት የመላች /2ሳሙ 6÷12/፣ ዳዊት የዘመረላት /2ሳሙ 6÷14/፤ ጠቢቡ ሰሎሞን በቤተ መቅደስ በክብር ያኖራት/1ነገ 8÷1/፤ የእግዚአብሔር የክብር መገለጫ ናት፡፡

በታቦተ ጽዮን እና በዘመነ ሐዲስ በተገለጠችው በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል ያለውን ረቂቅ እና ድንቅ ምስጢራዊ ንጽጽር አስመልክቶ ሦርያዊው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም፤ «ታቦት በወርቅ ልቡጥ እምኩለሔ ዘግቡር እምዕፅ ዘኢይነቅዝ፤ ከማይነቅዝ እንጨት የተቀረጸ በው ስጥ በአፍአ በወርቅ የተለበጠ 

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሐ ጠባይዕ ሳያድፍባትና የቅድስና ባሕርይ ሳይጎድፍባት በማየት፣ በመስማት፣ በመዳሰሰ፣ በማሽተት አንዳችም እድፍ ጉድፍ ሳያገኛት በንጽሕናና በቅድስና ጸንታ በኃጢአት ሳትለወጥ ኖራለች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም፤ «አልብኪ ነውር ወኢምንትኒ ላዕሌኪ፤ ምክንያታዊ ነውር ኃጢአት የሌለብሽ የኃጢአት ሸታ ያልደረሰብሽ ንጽሕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና ክብርት በልዕልና አንቺ ነሽ» /መኃ 4÷7/ ሲል ተናግሯል፡፡

ታቦተ ጽዮን በከበረ ወርቅ እንደተሸለመች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ እና በንጽሐ ልቡና የተሸለመች ያጌጠች መሆኗን ያጠይቃል፡፡

ታቦተ ጽዮን የቃለ እግዚአብሔር ማደሪያ እንደሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያምም ለአካላዊ ቃል ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያ ሆናለች፡፡ ይኽንንም ቅዱስ ኤፍሬም ሲያስረዳ፤ «ኮንኪ ታቦቶ ለፈጣሬ ሰማያት ወምድር ፆርኪዮ በከርስኪ ተሰዓተ አውርኃ አንቲ ማእምንት ለዘኢያገምርዎ ሰማያት ወምድር፤ ድንግል ማርያም ሆይ ሰማይና ምድርን ለፈጠረ አምላክ ለእርሱ ማደሪያ ሆንሽ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀንሸ ቻልሽው ተሸከምሽው ሰማይና ምድር የማይወስኑትን ለመወሰን የታመንሽ አንቺ ነሽ» ብሎ ተቀኝቶላታል፡፡ ስለሆነም ከብሉይ ኪዳን እስከ ሐዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ራሱን የገለጠበትን የቸርነት በዓል እግዚአብሔርበፈቀደልን ቦታ ሆነን ስናከብር ከእኛ የሚጠበቀውን በጎ ነገር እያሰብን በተግባርም እየገለጥን ከበዓሉ ረድኤትና በረከት ተሳታፊ እንሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የእናቱ የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

የቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እና ምልጃ አክሊልና ጉልላት በሆነው በእናታችን በወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት ሁላችንንም ይማረን፡፡


/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ህዳር 15-30 ቀን 2003ዓ.ም/



LIKE OUR PAGE >>>

https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl