Tuesday, January 8, 2013

ጥር 1



እነሆ  የተባረከ ወርሃ ጥር ባተ፤ ይህ ወር ቀኑ 14 ሰዓት ሌሊቱ 10 ሰዓት ነው። በዚህ ወር ታላላቅ በዓላት ይከበራሉ ከነዚህም መካከል፤ብርሃነ ጥምቀቱ፤ ግዝረቱ፤ ቃና ዘገሊላ፤ ቅድስት ስላሴ፤ የእመቤታችን እረፍት፤የቅዱስ ጊዮርጊስ ዝርዎተ አጽሙ፤ የዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ፤የነብዩ ኤልያስ፤የቅዱስ ኡራኤል ዓመታዊ በዓላቸው ሲሆኑ ሌሎችም ታላላቅ ቅዱስን አባቶች ታስበውና ተዘክረው ይውላሉ። እነሆ ጥር 1 ቀን የቀዳሚ ሰማዕት የሊቀ ዲያቆናት የቅዱስ እስጢፋኖስ የእረፍት ቀኑ ነው፤ የዚህ ሰማዕት ልደቱም በዚሁ ቀን ነው። በስሙ በታነጹለት አብያተ ክርስቲያናት ታቦተ ህጉ ወጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል፤ ዝነኛው ገዳሙ ሃይቅ እስጢፋኖስ በመዲናችን አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ የሚገኘው ደብሩ ከቀደምቶቹ አንዱ ነው። እስጢፋኖስ ማለት ወደብ ጸጥታ ማለት ሲሆን ቁጥሩ 72 አርድዕት ነው፤ ለምን ቀዳሚ ሰማዕት ተባለ ከሱ በፊት ሰማዕታት የሉም ነበርን ? ቢሉ መኖርስ አሉ የእርሱ ግን ቀዳሚ መባሉ ከጌታችን እርገት በኃላ ስለ ጌታችን መውረድ መወለድ መስክሮ የሞተ የመጀመሪያው እርሱ ስለሆነ ነው፤ እሺ ለምንስ ሊቀ ዲያቆናት ተባለ ቢሉ በሐዋርያት እጅ ከተሾሙት ሰባቱ ዲያቆናት ውስጥ የሁሉም አለቃ እርሱ ስለሆነ ነው ሐዋ 6 5 መጽሐፍ ቅዱስ ስለእስጢፋኖስ እንዲህ ሲል በእውነት መሰከረ "እስጢፋኖስም ጸጋንና ኃይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበረ...ፊቱም የመልአክ ፊት ይመስል ነበር   ይናገርበት የነበረውን ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ  አልቻሉም ሐዋ 6 8 እህሳ  አይሀድ አማጽያን መልስ መስጠት ቢያቅታቸው ድንጋይ አነሱ ልብ አናቱን እያሉ ወገሩት፤  ቀና ብሎ ቢመለከት ቅድስት ስላሴን አየ፤ አቤቱ ይህን ኃጢያት አትቁጠርባቸው ይቅር በላቸው እያለ  ነፍሱን ሰጠ። ሐዋ 7 60


ቅዱስ እስጢፋኖስ የተወለደው በኢየሩሳሌም በምትገኝ ሐኖስ በተባለች ቦታ ነው:: አባቱ ስምዖን ሲባል እናቱ ደግሞ ሐና ትባላለች ነገዱ ከነገደ ብንያም ነው :: የኦሪትን ሕግና ሥርዓት ከኦሪቱ ምሁር ከገማልያል ተምሯል::በሐዋርያት ሥራ ምዕ. 6 እንደምናነበው ሕዝቡን በማዕድ ያገለግሉ ዘንድ ሰባት ዲያቆናት ተመርጠዋል ከእነዚህ መካከል ቅዱስ እስጢፋኖስ አንዱ ሲሆን ለስድስቱ ዲያቆናት ደግሞ አለቃ( ሊቀ ዲያቆን) ሆኖ ተሹሟል ይህም የሆነው በጥቅምት 17 ነው ::
ቅዱስ እስጢፋኖስ በማዕድ አገልግሎት ሕዝቡን ከማገልገሉ በተጨማሪ ወንጌልን ይሰብክ ነበር ተአምራትን የማድረግ ጸጋም ተሰጥቶት ነበር በዚህም አገልግሎቱ ብዙዎችን ወደክርስትና መልሷል:: በዚህም አይሁድ በቅናት ተነሳስተው በሐሰት ከሰሱት ከከተማውም ወደ ውጭ አውጥተው ቄዳር በተባለ ቦታ በድንጋይ ወገሩት በሚወግሩትም ጊዜ ሰማያት ተከፍተው ምሥጢረ ሥላሴን (እግዚአብሔርን በሦስትነቱ ) ተመለከተ ኢየሱስ ክርስቶስንም በአብ ቀኝ ተቀምጦ አየ ለሚወግሩትም ሰዎች ከአምላኩ እንዲህ በማለት ምሕረትን ለመነ "ጌታ ሆይ ይህንን ኃጢአት አትቁጠርባቸው "በመጨረሻም "ጌታ ኢየሱስ ሆይ ነፍሴን ተቀበል" ብሎ ነፍሱን ሰጠ ::የሐዋርያት ሥራ ምዕ 7
በተወለደ 30 ዓመቱ 35 . በሰማዕትነት ዐረፈ::

ከሰማዕቱ በረከት ያሳትፈን።  

No comments:

Post a Comment