Friday, June 21, 2013

ሰኔ 12



 በዚህች ቀን ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል አፎምያን ከሰይጣን እጅ ያዳነበት ቀን ነው። ዳግመኛም በዛሬዋ ቀን ጻድቁ ንጉስ ቅዱስ ላሊበላ ያረፈበት ቀን ነው። ቅድስት አፎምያ የቅዱስ ሚካኤልን ዝክር ታዘክር ነበር ለድሆችም አብዝታ ትረዳ ነበር፤ በዚህ ሰይጣን ቀናባት በመነኩሴ ተመስሎ ሊያስታት ሞከረ በቅዱስ ሚካኤል ስዕል አሳፍራ መለሰችው ከ 3 ወራት በኃላ ሰኔ 12 ቀን ዳግመኛ ቅዱስ ሚካኤል ነኝ ብሎ ሊፈትናት መጣ፤ ሚካኤል ከሆንክ መስቀልህ የት አለ አለችው ከዚህ በኃላ አፉን ከፍቶ አይኑን አጉረጥርጦ አንገቷን አነቃት “ቅዱስ ሚካኤል ድረስልኝ” ብላ ተጣራች ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ፈጥኖ ወረደ በበትረ መስቀሉም መታው ጊዜዬ ሳይደርስ አታጥፋኝ ስዕልህ ባለበት፤ ስምህ በተጠራበት፤ ድርሳንህ በሚነበብበት፤ ፈጽሞ አልደርስም ብሎ ማለ፤ ተገዘተ ሸሸም፤ ከዚህ በኃላ ቅዱስ ሚካኤል ቅድስት አፎምያን “ወዳጄ አፎምያ ባነቺ ደስ አለኝ ወጋሽ በሰማይ ታላቅ ነው” ብሎ ባርኳት አርጓል። ቅዱስ ላሊበላ (ላልይበላል) ላል ማለት ማር ማለት ነው፤ሲወለድ በንብ ተከቦ ነበርና ማር ይበላል “ላልይበላል” አሉት ሚስቱ ቅድስት መስቀል ክብራ ትባላች እረፍቷ ሐምሌ 27 ነው ልጁ ይትባረክ እረፍቱ መስከረም 24 ቀን ነው ቅዱስ ላሊበላ 40 ዓመት ኢትዮጰያን አስተዳደረ ዓለምን የሚያስደንቅ እጹብ እጽብ የሚያሰኝ ከአንድ አለት ብቻ እጀታ በሌለው መጥረቢያ 12 ውቅር አብያተክርስቲያናትን አነጸ፤ እነዚህ በአንድ ቦታ ስላሉ ነው እንጂ በወሎ በጎንደር በሸዋ ለቁጥር የሚበዙ አብያተክርስቲያናትን አንጿል፤ ታህሳስ 29 ቀን ተወልዶ በ 80 ዓመቱ ሰኔ 12 በዛሬዋ ቀን አርፏል። መጨረሻ ያነጸው ቤተክርስቲያን አዳዲ ማርያምን ነው፤ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ናቸው እንዲያንጽ የጠየቁት እርሱም ጀምሮ ሳይጨርስ አቡነገብረመንፈስ ቅዱስ ወደርሱ ቀርበው ወዳጄ ላሊበላ የእረፍትህ ቀን ደርሷልና ወደ ላስታ ተመለስ አሉት እርሱም ተመለሰ በዚያም አረፈ፤ እራሱ ባነጸው በቤተ ጎሎጎታ ተቀበረ በመቃብሩም ላይ ለ 10 ቀን የማይጠፋ ብርሃን ሲበራ ይታይ ነበር። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

No comments:

Post a Comment