Wednesday, July 3, 2013

ሰኔ 26

ይህ ቀን የኢትዮጵያውያን የክረምት መጀመሪያ ነው። ገበሬው መሬቱን አርሶ አለስልሶ ዘሩን ለምድር አበድሮ በተስፋ ወደ ሰማይ ያንጋጥጣል እግዚአብሔር ዝናም እንዳይነሳው፤ የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል የእጅህንም በረከት ይጠባበቃል አለ ልበ-አምላክ ዳዊት መዝ 103፤ እግዚአብሔርም ቸር ነው አያሳፍርም ዝናም ለዘር ጠል ለመከር ይሰጣል፤ምድርም ቡቃያዋን ታበቅላለች፤ያበደሯትን ዘር በአንዱ ቅንጣት ሰላሳ ስድሳ መቶም እጥፍ ታፈራለች፤ ጻድቁ ኢዮብ እንጀራ ከምድር ውስጥ ይወጣል ያለው ይህንንም አይደል ኢዮ 28፤5። ይህ የክረምት ወራት ጭቃው ብርዱ ዶፉ መብረቅ ነጎድጓዱ ውሽንፍሩ ሁሉም ተባብረው የሰውን ልብ ያርዳሉ ያሸብራሉ። ይህም የኦሪት የዘመነ መርገም የዘመነ ፍዳ ምሳሌ ነው፤ አባቶች ክረምትን አልፈው የመስከረምን ጮራ ሲያዩ “እሞታለው ብዬ ስባባ እሰይ መስከረም ጠባ” ይላሉ የክረምቱን አስፈሪነት በሞት መስለውት፤ ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን የሙሴ ደቀ መዝሙር፤ እስራኤልን እየመራ ምድረ ግብጽ ያገባ፤ የአህዛብ ነገስታትን ድል የመታ፤ ጸሐይን በገባኦን ጨረቃንም በኤሎም ቆላ ያቆም፤ እያሱ በ120 ዓመቱ አረፈ፤ ። በረከቱን ያድለን።

No comments:

Post a Comment