Thursday, October 31, 2013

ጥቅምት 12

ወበዛቲ ዕለት...
ጥቅምት 12 በዚህች ቀን አባ ዲሜጥሮስ አረፈ፤ይህ አባት ያልተማረ ገበሬ ነበረ ይላል ስንክሳሩ፤ እንዲህም ሆነ በዚያን ወቅት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ የነበረው ዩልያኖስ የእረፍቱ ቀን ሲደርስ የታዘዘ መልአክ ተገልጾ ዛሬ የወይን ዘለላ ይዞ የሚመጣ ምዕመን አለ፤ ካንተ በኃላ ሊቀ ጳጳስ የሚሆነው እርሱ ነውና ተቀበለው ይለዋል፤ ዲሜጥሮስ ወደ ተክል ቦታው ሲገባ ያ
ለወቅቱ ያፈራ ወይን ያገኛል በጣም ተገርሞ ይህንንማ ለሊቀ ጳጳሱ ነው የምሰጠው ብሎ ይዞ ይሄዳል፤ አባ ዩልያኖስ መልአኩ የነገረውን ተረዳ እንደተባለውም አደረገ፤ አባ ዲሜጥሮስ ከሹመቱ በኃላ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ በርካታ መጽሀፍትን ደረሰ ከነዚህም ዋንኛው የአጽዋማትንና የበዓላትን ቀን የሚደነግገው ባህረ ሐሳብ የተሰኘው ግሩም መጽሀፍ አንዱ ነው። የሚገርመው ይህ አባት ከብቃቱ የተነሳ የሰዎችን ኃጢያት ያይ ነበር ሊቆርቡ ሲመጡ አንተ አልበቃህም ንስሀ ግባ አንተ በቅተሃል እያለ ያቆርብ ነበር፤ በዚህም ገሚሶቹ ጠሉት ፤ እርሱ ደግሞ ማነውና ጳጳስ ድንግል መሆን ሲገባው ሚስት አግብቶ እየኖረ የአባቶቻችንን ወንበር አረከሰ ብለውም አሙት፤ በዚህም የታዘዘ መልአክ ተገልጾ እራስህን ግለጽላቸው ይለዋል፤ እንደተባለውም ህዝቡ የደመራ እንጨት ይዞ እንዲመጣና ያመጣውን እንጨት እንዲነድ ያደርጋል፤ በሚነድ እሳት ውስጥም ገብቶ ለረጅም ጊዜ ይቆማል ሚስቱንም ይጠራታል እርሷም እሳት ውስጥ ትገባለች ፍሙን እያነሳ ይሰጣታል በቀሚሷ ትቀበለዋለች፤ የአገሬው ህዝብ ይህንን አይቶ እጹብ እጹብ አለ ምስጉን እግዚያብሔርንም አመሰገነ። ከእሳቱ ወጥቶ እንዲህ ይላቸዋል እኔ ይህን ያደረኩት ውዳሴ ከንቱ ሽቼ አይደለም በሐሜት እንዳትጎዱ ብዬ እንጂ ይህቺ የአጎቴ ልጅ ነች ከተጋባን 48 ዓመታችን ነው አንድ አልጋ ላይ እንተኛለን በግብረ ስጋ አንተዋወቅም ሁለታችንም ድንግል ነን አላቸው፤ ህዝቡ ተንበርክኮ ይቅርታ ጠይቆታል፡፡ አባ ዲሜጥሮስ ሸምግሎ ሳለ ህዝቡ በአልጋ ተሸክሞት ቤተክርስቲያን እየወሰደው እስኪመሽ አልጋ ላይ ተኝቶ ያስተምር ነበር፤ በንጽህና በቅድስና ኖሮ በ 107 ዓመቱ ጥቅምት 12 ቀን አርፏል። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን ወንጌልን የጻፈልን ሐዋርያው ማቴዎስ የእረፍት ቀኑ ነው፤ይህ ሐዋርያ ኢትዮጰያ መጥቶ ወንጌልን እንደሰበከ በርካታ መጽሐፍት ላይ ተጠቅሶ ይገኛል፤ የመልአክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ዳዊትን ቀብቶ እንዲያነግሰው ወደ ሳሙኤል የተላከበት ቀን ነው፡፡ የመልአኩንም የቅዱሳኑን በረከት ያድለን፡፡

LIKE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

No comments:

Post a Comment