Monday, July 14, 2014

ሐምሌ 8 እንኳን አደረሳችሁ

በዚህች ቀን ከሮም ነገስታት ወገን የሆነው አባ ኪሮስ አረፈ፡፡ አባታቸው በሞተ ጊዜ ታላቅ ወንድማቸው ቴዎዶሲዎስ በሮም ነገሰ፡፡ አባታችን አቡነ ኪሮስ ግን ሀብት ንብረታቸውን ትተው ወደ ገዳም ሄዱ ከአባ በቡኑዳ እጅም ምንኩስናን ተቀበሉ በታላቅ ተገድሎ ኖረው በዛሬዋ ዕለት በክብር አረፉ፡፡ አባታችን አቡነ ኪሮስ በመዲናችን አዲስ አበባ በኮተቤ መስመር በስማቸው ታላቅ ቤተክርስቲያን አላቸው ሐምሌ 8 ታቦታቸው ወጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል፡፡ ልጅ የሌላቸው እናትና እህቶቻችን ገድላቸውን አዝለው ልጅ እንዲሰጧቸው ስለት ይሳላሉ በዓመቱም ልጅ አዝለው መጥተው ስለታቸውን ይከፍላሉ፡፡ ይህንንም በአይናችን አይተን በጆሯችን ሰምተን ይኸው እንመሰክራለን ፡፡ በረከታቸው ይደርብን

LIKE OUR PAGE >>>

Sunday, July 13, 2014

ሐምሌ 7 እንኳን አደረሳችሁ


በዚህች ቀን አጋዕዝተ ዓለም ስላሴ በአብርሃም ቤት ተገኝተው ቤቱን የባረኩበት የአንድነታቸውንና ሶስትነታቸው ሚስጢር የገለጹበት ታላቅ በዓል ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን ሐምሌ 7 ዕረፍቱ ለአባ ሊባኖስ
ሲኖዳ ማለት ተአምኒ ምለት ነው። ሀገሩ እስክንድርያ ነው። አባት እናቱ ሠንላል የሚባል ቦታ ይኖሩ ነበር። አንድ ቀን እናቱ ውሃ ልትቀዳ ስትሄድ አባ ክርስሳርዮስ ደቀመዛሙርቱን አስከትሎ ሲሄድ አገኛት ቡርክት አንቲ ወቡሩክ ፍሬ ከርስኪ ለቀደሙት ቅዱሳን ወንድማቸው ለኋለኞችም አባታቸው የሚሆን ቡሩክ ፍሬ በማኅፀንሽ አለና የተባረክሽ ነሽ ብሎ 3 ጊዜ ራሷን ሳማት። ደቀመዛሙርቱ አባታችን ሴት አነጋግሮ አያውቅም ነበር ዛሬ ምን ሆኗል? አሉ ይህን አውቆ የልጇን ክብር ነግሯቸዋል።
ያደገው ያባቱን በጎች ሲጠብቅ ነው። ሌሊት መንጋውን አሰማርቶ እሱ ከጉድጓድ ገብቶ ሲጸልይ ያድር ነበር። አንድ አረጋዊ ከጉድጓድ ገብቶ ሲጸልይ አሥሩ ጣቶቹ እንደ ፋና ሲያበሩ አይቶ አባት እናቱን እንዲህ ያለ ደግ የወለዳችሁ ምን ብጹዓን ናችሁ አላቸው። እንዲህማ ከሆነ የእግዚአብሔር እንጂ የኛ አይደለም ብለው ለመምህር ሰጡት ሲሰጡትም ናሁ ይሰመይ አርስመቅሪዶስ ለኩሉ ዓለም እነሆ የባሕታውያን ራስ ይባላል የሚል ድምጽ ከወደላይ ተሰምቷል። ከዚህ በኋላ እየተማረ እያገለገለ በጾም በጸሎት ተወስኖ በትኅርምት ኗሪ ቢሆን መልአኩ የኤልያን አስኬማ የዮሐንስን ቅናት ሲሰጠው መምህሩ በራዕይ አየ በማግስቱም የሰጠሁህን ለሲኖዳ አልብሰው አለው መዓረገ ምንኩስና ሰጥቶታል።
በ431 ዓ.ም ለአውግዞተ ንስጥሮስ በቁስጥንጥንያ በተደረገው ጉባዔ ቅዱስ ቄርሎስን ተከትሎ ተገኝቷል። ንስጥሮስን አውግዘው ሃይማኖት መልሰው ሲመለሱ መርከበኞች ሊቀ ጳጳሳቱ በተሳፈረበት መርከብ አትሳፈርም ብለው ከለከሉት ጌታ ብሩህ ደመና አዞለት በዚያ ተጭኖ ሲሄድ በመርከቡ አንጻር ሲደርስ የመርከቡ ጣሪያ እንደመስታወት ሆኖላቸው እሱና ሊቀጳጳሳቱ ተያይተው እጅ ተነሣስተዋል። እኒያም ክብሩን አይተው ደግ ሰው አስቀይመናል ብለው ተጸጽተዋል። በመጨረሻም በስሙ ጥርኝ ውኃ ለደኃ እስከመስጠት ድረስ በጎ የሠራውን እንደሚምርለት ጌታ ቃል ኪዳን ሠጥቶት ሕማም ድካም ሳይሰማው በተወለደ በ120 ዓመቱ ዐርፏል። የጻድቁ ምልጃና በረከት በሁላችን ላይ አድሮ ይኑር አሜን።

ሐምሌ 6

በዚህች ቀን ዕዝራ ሱቱኤል ልክ እንደ አባቶቹ ሄኖክና ኤልያስ ሞትን ሳይቀምስ ወደ ብሄረ ህያዋን የተወሰደበት ቀን ነው፤ይህ ነብይ ቅዱስ ኡራኤል እሳት የመሰለ የጥበብን ጽዋ ካጠጣው በኃላ በባቢሎን ምርኮ ጊዜ ጠፍተው የነበሩትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በ 40 ቀናት ውስጥ በድጋሚ ጻፋቸው፤ በረከቱ ይደርብን

እንኳን አደረሳችሁ፤ ሐምሌ 5

በዚህች ቀን የቤተክርስቲያን አዕማድ የዓለም ብርሃን የሆኑት ሊቀ ሐዋርያ ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በሮም አደባባይ በኔሮን እጅ በሰማዕትነት አረፉ፤ ቀዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ ነፍሱ እስክትወጣ ለህዝቡ ወንጌልን ይሰብክ ነበር፤ ቅዱስ ጳውሎስን አንገቱን ሰይፈው ገደሉት፤ ሩጫቸውን ጨረሱ ሃይማኖታቸውንም ጠበቁ በዛሬዋ ዕለት የክብር አክሊልንም ተቀበሉ። በረከታቸው ይደርብን


ሐምሌ 4

በዚህች ቀን በይሁዳ ንጉሥ በአሞጽ ልጅ በኢዮስያስ ዘመን የነበረው ነብዩ ሶፎንያስ አረፍ፤ ይህ ነብይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትንቢተ ሶፎንያስን የጻፈው ነው፤ ስለ ኢትዮጰያም ደጋግሞ ትንቢቶችን ተናግሯል፤ "ከኢትዮጵያ ወንዞች ማዶ የሚማልዱኝ፥ የተበተኑት ሴቶች ልጆቼ፥ ቍርባኔን ያመጡልኛል" ሶፎ 3 ፤ 9-10። በረከቱ ይደርብን፤

ሐምሌ 3

በዚህች ቀን ታላቁ የቤተክርስቲያን ሊቅ አባ ቂርሎስ አረፈ። ይህ ሊቅ አገሩ ሶርያ ነው፤ ግን ልብ በሉ የእስክንድርያ 23ኛ ጳጳስ ሆኖ ተሹሟል። ልክ ነው እንደዚያ ነበራ በደጉ ዘመን ከየት ነህ ከወዴት መጣህ አይሉም አጥንት አይቆጥሩም ደም አያንቆረቁሩም ነበር፤ ቅድስናው እውቀቱ ስንምግባሩ ከተመሰከረለት፤ ለመሾም የአዳም ዘር ብቻ መሆን ይበቃል። እሺ አባ ቂርሎስ መናፍቁ ንስጥሮስን ተከራክሮ የረታ ድንቅ አባት ነው፤ ቀድሞ ንስጥሮ የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ ነበር፤ መቼም አያድርስ ነው ይህ ጳጳስ ሳተ ተሳሳተ አሳሳተ እመቤታችን ወላዲተ አምላክን ወላዲተ ሰብ እንጂ ወላዲተ አምላክ አይደለችም አለ፤ ለዚህም ጉባዬ በኤፌሶን ከተማ ተደረገ፤የወቅቱ ንጉስ ቴዎዶስዮስ ነበር፤ የተሰበሰቡት ሊቃውንት ደግሞ 200 ናቸው ሊቀ መንበሩ ቂርሎስ ነው፤ ክርክሩ ተጀመረ፤ አባ ቂርሎስ እንደ ሰይፍ የሚቆራርጡ ቃላትን ከመጽሐፍ ቅዱስ እያጣቀሰ መወርወር ጀመረ፤ ንስጥሮስ የሚመልሰው አጣ ተረታ፤ ወደ ቀደሞ ሃይማኖትህ ተመለስ አሉት አልመለስም ብሎ ወደ ላይላይ ግብጽ ይሰደዳል፤ ቂርሎስ መልካም ባልንጀራው ነበርና ተከትሎት ሄዶ ይመክረዋል ወንድሜ ንስጥሮስ የያዝከው መንገድ ስህተት ነው፤ እመቤታችንን ወላዲተ አምላክ ነች ልጇም የባህርይ አምላክ ነው በል ይለዋል፤ መቼም ያዲያቆነ ስየጣን ነውና አልልም ብሎ ይመልስለታል፤ እንግዲያውስ ለኔ እንዳልታዘዘክ አንደበትህ አይታዘዝህ ብሎ ይረግመዋል ወዲያውኑ ምላሱ ተጎልጉሎ ወጣ ደምና መግል እየተፋ ተቀብዝብዞ ሞቷል። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ የአሁኑ የአዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቀውስጦስ በአንድ ወቅት ተመሳሳይ ተአምር አድርገዋል ቦታው በዚሁ በምዕራቡ የአገራችን ክፍል በአንድ ቤተክርስቲያን አውደ ምህረት ላይ ቆመው ሲያስተምሩ አንድ መናፍቅ ተንደርደሮ አውደ ምህረቱ ላይ ይወጣና በልሳነ መናገር ይጀምራል አቡነ ቀውስጦስም ወንድሜ መስበክ ከፈለክ ሁላችንም በምንሰማው ቋንቋ ተናገር ይሉታል መረበሽ ጀመረ ቢመክሩት እምቢ አለ እንግዲያውስ ወላዲተ አምላክ አንደበትህን ትዝጋው ይሉታል ወዲያው አንደበቱ ተያዘ መናገር ተሳነው፤ ከዚያ በኃላ የአገር ሽማግሌዎች ተሰብስበው እግራቸው ላይ ወድቀው አባታችን ይማሩት አሏቸው፤ ጸሎት አድርገው አንደበቱን ፈተውታል፤ ይህ እውነት ነው፤ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ፤ አባ ቂርሎስ በርካታ መጽሐፍትን ጽፏል ከነዚህም አንዱ ቅዳሴ ቂርሎስ ነው ሃይማኖተ አበው ላይም ስለ መለኮት ገራሚ ገራሚ ነገሮች ተናግሯል፤ 32 ዓመት በማርቆስ መንበር መንጋውን በፍቅር ጠብቆ ሐምሌ በባተ በ 3ኛው ቀን አርፏል። በረከቱ ይደርብን፤ ቅዳሴ አንድምታ፤ ስንክሳር። በረከቱን ይደርብን።

ሐምሌ 2

በዚህች ቀን ከ 12ቱ ሐዋርያት አንዱ የሆነው ሐዋርያው ታዲዎስ አረፈ። ዓለምን ዞራችሁ ለፍጥረት ሁሉ ወንጌልን ስበኩ በተባሉት መሰረት ሐዋርያት ዓለምን በእጣ ሲከፋፈሉ ለዚህ ሐዋርያ ሶርያ ደረሰችው፤ ዛሬ የእርስ በእርስ እልቂት ያለባት አገር፤ ይህ ሐዋርያ እጅግ ድንቅ ታአምራት በሶርያ ምድር አድርጓል፤ ነገሩ እንዲህ ነው፤ አንድ ትዕቢተኛ ሰይጣን ያደረበት ባለጸጋ ቀርቦት መምህር ሆይ በመጽሐፍ ቅዱሳችሁ ሀብታም መንግስተሰማያት ከሚገባ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ይላል፤ እስኪ መጽሐፍ ቅዱሳችሁ እውነት ከሆነ አድርገህ አሳየን ይለዋል፤ ሐዋርያው ታዲዎስም መርፌ የሚሰራ ባልንጀራ ነበረውና መርፌ እንዲልክለት ሰው ይሰዳል ያ መርፌ ሰሪም ሐዋርያውን ለመርዳት አስቦ ቀዳዳውን ትንሽ አስፍቶ ይልክለታ፤ ታዲዎስም ፈገግ አለ የመርፌ ቀዳዳ ምን ቢሰፋ እንዴት ግመል ያሳልፋል ስለውለታህ አመሰግናለው ትክክለኛውን መርፌ ላክሊኝ ብሎ ይመልስለታል እርሱ ድጋሚ አስተካክሎ ይልክለታል፤ ከዚህ በኃላ አገሬው በአደባባይ ተሰበሰበ ጭነት የያዘች ግመልና አንድ ነጋዴም ተዘጋጁ ሐዋርያው ዓይኑን ወደ ሰማይ ቀና አድርጎ አምላኬ ሆይ ይህን የማደርገው ክብርህ እንዲገለጽ እንጂ ክብሬ እንዲገለጽ ብዬ አይደለም ጸሎቴን ስለሰማኸኝ አመሰግንሃለው አለ፤ ጸሎቱን እንደጨረሰ ጭነት የተሸከመችውን ግመል እንድታልፍ አደረጋት ሰው ሁሉ እያያ በመርፌው ቀዳዳ ሾለከች አገሬው እልልታውን አቀለጠው ለሁለተኛ ጊዜ ለሶስተኛ ጊዜም እንድትሾልክ አደረገ፤ ህዝቡ ይህን የእግዚያብሔር ድንቅ ተአምራት አይቶ ብዙዎች አመኑ ተጠመቁም፤ ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ እንደዚህ ያለ ተአምራት ያየ ማን አለ እኛ ግን ከሶርያ ህዝብ ጋር አየን ተመለከትን፤ በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ እንዳለ " በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ያደርጋል ከእኔም በላይ ያደርጋል" ግሩም ነው የፈጣሪ ስራ። ሐዋርያው ቅዱስ ታዲዎስ በብዙ አገር ተዘዋውሮ ሲያስተምር ጣኦት አምላኪዎች ይዘው አሰቃዩት በዛሬዋ ቀንም ገድለውታል እርሱም የሰማዕትነት አክሊል ተቀብሏል። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከሐዋርያው በረከት ያሳትፈን። ስንክሳር፤ ገድለ ሐዋርያት።

ሰኔ 30

በዚህች ቀን የጌታን መንገድ ጠራጊው፤ሐዋርያው፤ነብዩ ሰማዕቱ ቅዱስ ዮሐንስ የልደት ቀኑ ነው፤ መስከረም 2 አንገቱ የተቆረጠበት ነው ሚያዚያ 15 እረፍቱ ነው፤ አንገቱ ከተቆረጠ በኃላ የተቆረጠች አንገቱ ክንፍ አውጥታ ለ15 ዓመት በሳውዲአረቢያና አካባቢው ወንጌልን ሰብካለች፤ የካቲት 30 ቀን የዮሐንስ ራስ የተገለጸችበት ቀን ነው። ከነዚህ አራት በዓላት ሁለቱን ቤተክርስቲያን ታቦተህጉን አውጥታ በደማቁ ታከብረዋለች እነዚህም ሰኔ 30 ልደቱና መስከረም ሁለት አንገቱ የተቆረጠበትን ቀን ነው።ጨካኝ ሄሮድስ የቤቴልሔም ህጻናትን ሲጨፈጭፍ መጥምቁ ዮሐንስ ከአናቱ ከቅድስት ኤልሳቤጥ ጋር ወደ ሲና በርሃ ተሰደደ፤ኤልሳቤጥ በጣም አርጅታ ነበር ያን በርሃ ታዲያ እንዴት ቻለችው ያውም ልጅ አዝላ ልጅ ተሸክማ ረዳት ሳይኖራት ብቻዋን፤አባቱ ዘካርያስ በምኩራብ በመሰዊያው ፊት ልጅህን አምጣ ብለው አንገቱን ቆርጠው ገደሉት። ኤልሳቤጥም ሲና በርሃ ላይ ሞተች ህጻኑ ዮሐንስ ብቻውን ቀረ፤ የእናቱን በድነ ስጋ አቅፎ አለቀሰ፤ሁሉን ቻይ ሁሉን የሚያይ፤ ሁሉን የሚመረምር ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ለእመቤታችን እናቴ ሆይ ዘመድሽ ኤልሳቤጥ በበርሃ አርፋለች እንቀብራት ዘንድ እንሂድ አላት ደመና ጠቅሰው ዮሴፍና ሰሎሜን አስከትለው ሄደዋል ገንዘውም ቀብረዋታል፤ ከዚህ በኃላ እመቤታችን ልጄ ወዳጄ ሆይ ዮሐንስን ይዘነው እንሂድ አለችው የለም እናቴ ፤እርሱ እዚው ይቆያል መንገዴን ጠራጊ ነው፤ ኑሮው በዚሁ በርሃ ነው፤ጊዜው ሲደርስ ወደ ዮርዳኖስ ይመጣል ያጠምቀኝማል ያኔ አንድነቴ ሶስትነቴ ይገለጣል አላት፤ ትተውት ተመለሱ ከመሞቱ በፊት እናቱ ያሰፋችለትን የግመል ቆዳ አገልድሞ አንቦጣ የሚባል ቅጠልና የበርሃ ማር እየበላ በበርሃ ኖረ 30 ዓመት ከ 6 ወር ሲሆነው፤ “የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ” እያለ ከበርሃ ወጣ ሉቃ 3፤3። "እውነት እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤" ማቴ 11፤11። ይህ የጌታችን ምስክርነት ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

ሰኔ 29



ይህ ቀን የጌታችን የእየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ ነው፤ አባቶቻችን ባዘዙት መሰረት የቤተክርስቲያን ልጆች በየወሩ ልክ እንደ እሁድ ሰንበት አክብረውት ይውላሉ፤ልጁን ለላከ ለአብ ለተላከ ለወልድ ማህያዊ ለሚሆን መንፈስ ቅዱስም ክብር ምስጋና ይሁን።

Thursday, July 3, 2014

ሰኔ 27

ሰኔ 27 በዚህች ቀን ታሪኩ በሐዋርያት ስራ ምዕራፍ 9፤10 ላይ የተጠቀሰው ሐዋርያው ሐናንያ አረፈ። ቀድሞ ሳኦል የተባለው ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ሲያሳድድ ድንገት በደማስቆ ታላቅ ብርሃን ይመታዋል በምድር ይወድቃል ዓይኑም ይታወራል፤ “ሳውል ሳውል ስለምን ታሳድደኛለህ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል ይለዋል፤ ለ 3 ቀን 3 ሌሊት ዓይነስውር ሆኖ ይቆያል።ከዚያም የዛሬዋን ቀን መታሰቢያውን የምናደርግለት ሐዋርያው ሐናንያ እጁን ጭኖ ጸለየለት ዓይኑንም አበራለት ከዚያ በኃላ ነው ቅዱስ ጳውሎስ የቤተክርስቲየን ምርጥ እቃ የሆነው። ሐዋርያው ሐናንያ በደማስቆ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት ወንጌልን ሰብኮ ብዙዎችን ወደቀናች ሀይማኖት መለሳቸው፤የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ከዚህ በኃላ አረመኔው ንጉስ ሉክያኖስ ይዞ ብዙ መከራ አደረሰበት፤ አስገረፈው፤ በእሳት አቃጠለው፤ በፍላጻ አስነደፈው፤ በመጨረሻም በዛሬዋ ቀን በድንጋይ አስወግሮ ገድሎታል። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ በሉቃስ ወንጌል 16፤20 ታሪኩን የተናገረለት ዓልአዛር አረፈ። እንዲህ ይላል “… አልዓዛርም የሚባል አንድ ድሀ በቍስል ተወርሶ በደጁ ተኝቶ ነበር፥ ከባለ ጠጋውም ማዕድ ከሚወድቀው ፍርፋሪ ሊጠግብ ይመኝ ነበር፤ ውሾች እንኳ መጥተው ቍስሎቹን ይልሱ ነበር። ድሀውም ሞተ፥ መላእክትም ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት ይላል የዚህ ጻድቅ እረፍቱ ዛሬ ነው፤ ይህም ሰኔ 27 የሚነበበው ስንክሳር ላይ ተጽፏል።ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም የአባቶቻችንን በረከት ያሳትፈን። 
LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 25

ሰኔ 25 
በዛሬዋ ቀን ከሰባሁለቱ አርድእት አንዱ የሆነው የፀራቢው የዮሴፍ ልጅ ሐዋርያው ይሁዳ አረፈ፡፡ ይህ ሐዋርያ በመጽሐፍ ቅዱስ አንድ ምዕራፍ ብቻ ያለው የይሁዳ መልዕክትን የጻፈ ነው፤ በተለያዩ አገሮች በመዞር ህዝቡን ከአምልኮተ ጣኦት ወደ አምልኮተ እግዚያብሔር መለሰ ብዙዎችንም ክርስቲያን አደረገ፤ በመጨረሻም ሐራፒ በሚባል አገር ገብቶ ሲያስተምር ጣኦት አምላኪዎች ይዘው አሰቃዩት፤ሰቀሉት በዛሬዋም ቀን በፍላጻ ነድፈው ገደሉት፤ቅድስት ነፍሱን ሰጠ፡፡ በረከቱ ይደርብን
LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 24

ሰኔ 24 በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አባ ሙሴ ጸሊም አረፈ፡፡ አስቀድሞ ሽፍታ ወንበዴ ዘማዊ ጣኦት አምላኪ ነበር፤ በኃላ እንደ አብርሃም አምላኬ ማን ነው ብሎ ተመራመረ፤ ወደ አስቄጥስ ገዳም ብትሄድ አምላክህ ማን እንደሆነ ይነግሩሃል የሚል ራዕይ አየ ተመለከተ፤ ተነስቶም ሄደ አባ ኤስድሮስን አገኛቸው፤አጽናንተው አረጋግተው ወደ አባ መቃርስ ወሰዱት አባ መቃርስም ንስሃውን ተቀብለው ቀኖና ሰጡት ኃላም አመነኮሱት የሽፍቶች አለቃ የነበረው የመነኮሳት አለቃ እስከመሆን ደረሰ፤ ሰይፉን ወርውሮ ከፍቅር ጋር ተወዳጀ፤ሌሊት እየተነሳ ለሁሉም መነኮሳት ውኃ ይቀዳላቸው ነበር ሉሉም ይታዘዛቸው ነበር ትንሹም ትልቁም ሙሴ ይህን አድርግሊኝ ይሉታል አርሱም ሁሉንም እሺ ይላል፤ ራሱን ዝቅ አደረገ ትሁትም ሆነ፤ በጸሎቱ ዝናብ ያዘንብ ነበር፤ እድሜው መጨረሻ አካባቢ ቡራኬ ሊቀበል ከመነኮሳት ጋር ሆኖ ወደ አባ መቃርስ ሄደ አርሳቸውም ልጆቼ ከናንተ መካከል በሰማእትነት የሚሞት አለ ብለው ትንቢት ተናገሩ ሙሴ ጸሊምም አባቴ ያ ሰው እኔ ነኝ ሰይፍ የሚያነሱ በሰይፍ ይጠፋሉ የሚል ቃል አለ ይህን ጊዜ በጉጉት ስጠባበቀው ነበር አላቸው፤ እንደተባለውም የበርበር ሰዎች ገዳሙን ሊያጠፉ መጡ መነኮሳቱ ሲሸሹ ሙሴ እዚያው ቀረ ሌሎች ሰባት መነኮሳት ከአባታችን ጋር እንሞታለን ብለው አብረውት ሆኑ የበርበር ሰዎች ደረሱ ሁሉንም በሰይፍ ገደሏቸው፤ ይህም ሰኔ 24 ቀን ነው፤ የአባታችን የሙሴ ጸሊም ስጋው በገዳመ አስቄጥስ በክብር ይገኛል፤ ግብጻውን ቤተክርስቲያን ሰርተውለት ታቦት ቀርጸውለት በደንብ ያከብሩታል ገድሉን ጽፈውለታል ፊልምም ሰርተውለታል ይህን ፊልም የኛ ሰዎች ግሩም አድርገው ወደ አማርኛ መልሰውታል፡ የቻለ ገድሉን ያንብብ ያልቻለም ፊልሙን ይመልከተው፤ የዛሬዋን ቀን ስለ ተክለሃይማኖት ብቻ በለን አንመጽውት ስለ ሙሴ ጸሊምም እያልን ይሁን፤ አምላከ ተከልዬ ጠብቀኝ ስንል አምላከ ሙሴ ጸሊም አትርሳኝ ማለትን አንርሳ ይህ ድንቅ አባት የማይረሳ ነውና፡፡ ሙሴ ጸሊም ማለት ሙሴ ጥቁር ሰው ማለት ነው፤ መልኩ ጥቁር ስለሆነ ነው ጥቁሩ ሙሴ ተብሎ የተጠራው፤ እገሌ ጥቁር ሰው እገሌ ጥቁር ስው አሁን የመጣ አይደለም፤ ኳስ መቶ ጎል ያገባ በሙሉ እገሌ ጥቁር ሰው መባል ጀምሯል፤ ቤተክርስቲን ግን ጥንቱንም ቢሆን አንዱን ቅዱስ ከአንዱ ለመለየት ቅጽል ስም ትሰጣለች ለምሳሌ ዮሐንስ አጺር አጭሩ ዮሐንስ ስምኦን ጫማ ሰፊው ሙሴ ጸሊም ጥቁሩ ሰው ሙሴ……ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፡፡
LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 23

ሰኔ 23 
በዚህች ቀን የዳዊት ልጅ የቤርሳቤህ ልጅ ጠቢቡ ሰሎሞን አረፈ። በ 12 ዓመቱ ሲነግስ እግዚያብሔርን አንዲት ነገር ለመነው ፍርድ እንዳልገመድል ደሃ እንዳልበድል ጥበብን ስጠኝ ብሎ የልቡን መሻት ሰጠው ፍጹም ጠቢብም አደረገው፤ለ 40 ዓመት በቅን እየፈረደ በንግስና ቆይቶ በ 52 ዓመቱ በዛሬዋ ቀን አረፈ።

LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 20

ሰኔ 20 ከእመቤታችን 33ቱ በዓላት አንዱ ነው፤ህንጸተ ቤተክርስቲያን ይባላል። የመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን የታነጸው በዛሬዋ ቀን ነው አናጺውም እራሱ ባለቤቱ ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ቦታው ፊልጰስዩስ ነው፤ ቤተክርስቲያኗ የተሰየመችው ደግሞ በእመቤታችን ስም ነው። ጴጥሮስ፤ ዮሐንስ በርናባስና ሌሎችም ሐዋርያት በፊልጰስዩስ ተሰብስበው ሳለ ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ በኪሩቤል ጀርባ ላይ ሆኖ እልፍ አእላፍ መልአክትን አስከትሎ ይወርዳል እመቤታችን በቀኙ ነበረች፤ 3 ድንጋዮችን አንስቶ ጎተታቸው እንደ ሰም ተለጠጡ እንደ ግድግዳም ሆኑ ዳግመኛም የብርሃን ምሰሶ ወረደ በሰማያዊቷ እየሩሳሌም እምሳያ አድረጎ አነጻት ሁለንተናዋም ተጠናቀቀ፤ ዳግመኛ በበነጋው ሰኔ 21 ቀን እመቤታችንን እና ቅዱሳን መልአክትን አስከትሎ ይወርዳል ቅዳሴ ቀድሶ ለሐዋርያቱ አቆረባቸው ፍጹም ደስታም ሆነ። ከዚህ በኃላ ሐዋርያት ከጌታ እንዳዩት በዓለም ዞረው ቤተክርስቲያን አንጸዋል። ከዚያ በፊት የነበረው የነሶሎሞን ቤተመቅደስ የአይሁድ ምኩራብ የአይሁድ ስርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ እንጂ የአዲስ ኪዳን የቁርባንም ሆነ የጥምቀት ስርዓት መፈጸሚያ አልነበረም፤ ታዲያ ሐዋርያት የት ነበር ህዝቡን የሚያጠምቁት የሚያቆርቡት ካሉ በየሰው ቤት ነበር። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን ታላቁ ነብይ ኤልሳዕ አረፈ። ይህ ነብይ በ 12 ጥማድ በሬ ሲያርስ ቴስቢያዊው ነብዩ ኤልያስ ተከተለኝ አለው ምንም ሳያቅማማ ሀብት ንብረቱን ትቶ ተከተለው፤ ኤልያስ በእሳት ሰረገላ ከማረጉ በፊት ምን እንዳደርግልህ ትፈልጋለህ ይለዋል ባንተ ላይ ያደረ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እጥፍ ድርብ ሆኖ ይደርቢኝ ይለዋል፤ እንደ ቃሉ ሆነለት ተደረገለት፤ ኤልያስ አንድ ሙት ሲያስነሳ ኤልሳዕ ሁለት ሙት አስነስቷል፤ ኤልያስ አንድ ጊዜ ባህር ሲከፍል ኤልሳዕ ሁለት ጊዜ ባህር ከፍሏል። እምቤታችንን የኤልሳዕ ጋን ይላታል ኤልሳ የመረረውን ውኃ እንዳጣፈጠ እመቤታችንም ይህን መራራ ዓለም ጌታን በመውለዷ አጣፍጣዋለች፤ የዚህ ነብይ ድንቅ ታሪኩ 2ኛ ነገስት ላይ በስፋት ተጽፏል ሰኔ 20 ቀን እረፍቱ ነው ቤተክርስቲያን የዛሬውን ቀን እመቤታችንን እና ነብዩን አስባ ትውላለች። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 12

ሰኔ 12 በዚህች ቀን ሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል አፎምያን ከሰይጣን እጅ ያዳነበት ቀን ነው። ዳግመኛም በዛሬዋ ቀን ጻድቁ ንጉስ ቅዱስ ላሊበላ ያረፈበት ቀን ነው። ቅድስት አፎምያ የቅዱስ ሚካኤልን ዝክር ታዘክር ነበር ለድሆችም አብዝታ ትረዳ ነበር፤ በዚህ ሰይጣን ቀናባት በመነኩሴ ተመስሎ ሊያስታት ሞከረ በቅዱስ ሚካኤል ስዕል አሳፍራ መለሰችው ከ 3 ወራት በኃላ ሰኔ 12 ቀን ዳግመኛ ቅዱስ ሚካኤል ነኝ ብሎ ሊፈትናት መጣ፤ ሚካኤል ከሆንክ መስቀልህ የት አለ አለችው ከዚህ በኃላ አፉን ከፍቶ አይኑን አጉረጥርጦ አንገቷን አነቃት “ቅዱስ ሚካኤል ድረስልኝ” ብላ ተጣራች ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ፈጥኖ ወረደ በበትረ መስቀሉም መታው ጊዜዬ ሳይደርስ አታጥፋኝ ስዕልህ ባለበት፤ ስምህ በተጠራበት፤ ድርሳንህ በሚነበብበት፤ ፈጽሞ አልደርስም ብሎ ማለ፤ ተገዘተ ሸሸም፤ ከዚህ በኃላ ቅዱስ ሚካኤል ቅድስት አፎምያን “ወዳጄ አፎምያ ባነቺ ደስ አለኝ ወጋሽ በሰማይ ታላቅ ነው” ብሎ ባርኳት አርጓል። ቅዱስ ላሊበላ (ላልይበላል) ላል ማለት ማር ማለት ነው፤ሲወለድ በንብ ተከቦ ነበርና ማር ይበላል “ላልይበላል” አሉት ሚስቱ ቅድስት መስቀል ክብራ ትባላች እረፍቷ ሐምሌ 27 ነው ልጁ ይትባረክ እረፍቱ መስከረም 24 ቀን ነው ቅዱስ ላሊበላ 40 ዓመት ኢትዮጰያን አስተዳደረ ዓለምን የሚያስደንቅ እጹብ እጽብ የሚያሰኝ ከአንድ አለት ብቻ እጀታ በሌለው መጥረቢያ 12 ውቅር አብያተክርስቲያናትን አነጸ፤ እነዚህ በአንድ ቦታ ስላሉ ነው እንጂ በወሎ በጎንደር በሸዋ ለቁጥር የሚበዙ አብያተክርስቲያናትን አንጿል፤ ታህሳስ 29 ቀን ተወልዶ በ 80 ዓመቱ ሰኔ 12 በዛሬዋ ቀን አርፏል። መጨረሻ ያነጸው ቤተክርስቲያን አዳዲ ማርያምን ነው፤ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ናቸው እንዲያንጽ የጠየቁት እርሱም ጀምሮ ሳይጨርስ አቡነገብረመንፈስ ቅዱስ ወደርሱ ቀርበው ወዳጄ ላሊበላ የእረፍትህ ቀን ደርሷልና ወደ ላስታ ተመለስ አሉት እርሱም ተመለሰ በዚያም አረፈ፤ እራሱ ባነጸው በቤተ ጎሎጎታ ተቀበረ በመቃብሩም ላይ ለ 10 ቀን የማይጠፋ ብርሃን ሲበራ ይታይ ነበር። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።


LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 11

በዚህች ቀን ከሰባቱ ዓበይት ሰማዕታት አንዱ የሆነው ሰማዕቱ ቅዱስ ገላውዲዎስ አረፈ። ስንክሳሩ የመልአክት አርአያ ያለው ይለዋል ንጽህናውን ቅድስናውን ሲያጠይቅ፤ የሮም የነገስታት ልጅ ነው ዓለምን ክብሩን ሁሉ ንቆ ወጣ በፍጹም ተጋድሎም ኖረ ለጣኦት አልሰግድም አልሰዋም ብሎ ሰው ሊሰማው የሚከብድ ጽኑ መከራዎችን በትእግስት ተቀበለ በዛሬዋ ቀንም አንገቱን ተቆርጦ በሰማዕትነት አረፈ። ሰኔ 11 ቀን የሚነበበው ስንክሳር ታሪኩን በሰፊው ጽፎታል፤ ሊቀ ብርሃናት መርቆርዮስ አረጋ ይህ ሰማዕት በተለይም በጎንደር ልዩ ክብር እንዳለውና በስሙ ታላላቅ ገዳማት እንደታነጹለት በአጠቃላይ ኢትዮጰያ ውስጥ ከ 16 የማያንሱ አብያተክርቲያናት እንዳሉት “የቅዱሳን ታሪክ” በሚለው መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል፤ በነገራችን ላይ በዚሁ ስም የሚጠሩ ታላቅ የኢትዮጰያ ጻድቅ ንጉስም አሉ ዓጼ ገላውዲዎስ ግራኝ መሐመድን ድል የነሱ ናቸው ቤተክርስቲያን መታሰቢያቸውን መጋቢት 27 ቀን ታከብረዋለች። የዲያቆን ዳንኤል ክብረትን የቤተክርስቲያን ማረጃዎች የሚለውን መጽሕፍ ይመልከቱ ።ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 9

ሰኔ 9 በዚህች ቀን ከተራራማው ከአፍሬም አገር አርማቴም ከተባለ ቦታ የወጣው የሐና ልጅ ታላቁ ነብይ ሳሙኤል አረፈ። ይህ ነብይ በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ገልአርታ ውስጥ ታቦት እንዳለው ሊቀ ብርሃናት መርቆርዮስ አረጋ የቅዱሳን ታሪክ በሚለው መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል። ነብዩ ሳሙኤል በብዙ እንባ በታላቅ ትዕግስት የተገኘ ነብይ ነው ሐና መካን ሆና ለረጅም ዘመን ታለቅስ ነበር ሰዎችም ይዘባበቱባት ነበር ይህች የበቅሎ ዘመድ ቢወልዷት እንጂ የማትወልድ በኃጢያቷ ብዛት እየው እግዚያብሔር ልጅ ነሳት፤ደግሞ እኮ አታፍርም ወደ ቤተ እግዚያብሔር ትሄዳለች ይሏት ነበር፤ ከእለታት በአንዱ ቀን እጇን ወደላይ አንስታ ከንፈሯን እያንቀሳቀሰች በለሆሳስ እያለቀሰች ስትጸልይ ተመልክቶ ካህኑ ዔሊ ሳይቀር አንቺ ሰካራም በሎ ዘለፋት 1ኛ ሳሙ 1፤14። እግዚያብሔር ግን ጸሎቷን ሰማት እንባዋን አበሰላት ከልጅ በላይ ልጅ ሰጣት እርሷም እንዲህ ብላ ግሩም ምስጋና አመሰገነች ይህንን የሐና ምስጋና ቤተክርስቲያን ዘወትር ትጠቀምበታለች መዝሙረ ዳዊት የጸሎት መጽሐፍ ካልዎት ይህንን ምስጋና እዚያ ላይ ያገኙታል፤ ልቤ በእግዚአብሔር ጸና ቀንዴ በእግዚአብሔር ከፍ ከፍ አለ አፌ በጠላቶቼ ላይ ተከፈተ በማዳንህ ደስ ብሎኛል። እንደ እግዚአብሔር ቅዱስ የለምና፥ እንደ አምላካችንም ጻድቅ የለምና ከአንተ በቀር ቅዱስ የለም። አትታበዩ፥ በኩራትም አትናገሩ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና፥ እግዚአብሔርም ሥራውን የሚመዝን ነውና፥ ከአፋችሁ የኵራት ነገር አይውጣ። የኃያላንን ቀስት ሰብሮአል፥ ደካሞችንም በኃይል ታጥቀዋል። ጠግበው የነበሩ እንጀራ አጡ ተርበው የነበሩ ከራብ ዐርፈዋል መካኒቱ ሰባት ወልዳለችና፥ ብዙም የወለደችው ደክማለች። ኡፈየው እንዴት ያለ ጣፋጭ ምስጋና ነው፤1ኛ ሳሙ 2፤1። ነብዩ ሳሙኤል ሳኦልን ከአህያ ጠባቂነት ጠርቶ በእስራኤል ላይ ያነገሰ ነው ዳዊትን ደግሞ ከእረኝነት ጠርቶ ለእስራኤል ያነገሰ ነው፤ ሳኦልን በእስራኤል ዳዊትን ለእስራኤል “በ” እና “ለ” የእነዚህን ቃላት ልዩነት የሐሙስ ውዳሴ ማርያም አንድምታው ላይ በስፋት ተጽፏል፤ ነብዩ ሳሙኤል በ 98 ዓመቱ አረፈ እስራኤልም ሁሉ ተሰብስበው አለቀሱለት፥ በአርማቴምም በቤቱ ቀበሩት። 1ኛ ሳሙ 25፤1

LIKE OUR PAGE >>>

ሰኔ 8


ከእመቤታችን ሠላሳ ሦስቱ ባዓላት አንዱ ነው፤ በዚህ ዕለት ልጇ ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ግብጽ በስደት ሳሉ ለህሙማን ድህነት እንዲሆን ውኃን ከዓለት ላይ ያፈለቀበት ቀን ነው፤በዚሁ ቦታ በእመቤታችን ሥም ታላቅ ቤተክርስቲያን ተሰርቶ የተከበረበትም ቀን ነው፡፡እመቤታችንን ከፍጥረት ዓለም ለይቶ አክብሮ የእናት አማላጅ አድርጎ የሰጠን እግዚያብሔር ይመስገን፡፡
ከተአምር አስቀድሞ ይህ ይነበብ ህዝቡ ዕዝነ ልቦናቸውን ከፍተው ይስሙ፤ በዕብራይስጥ ማርያም የተባለች የእመቤታችንን ተአምር ለመስማት ቀላል አይምሰለው የከበረ ገናና ነውና ወደ ግዝት እንዳይገቡ መስማትን አያስታግሉ ፤ በእመቤታችን ሠላሳ ሦስቱ ባዓላትና እሁድ በተባለች ሰንበት ወንዶችም ሴቶችም ወደ ቤተክርስቲያን ይሰብሰቡ የተአምሯን መጽሐፍም ያንብቡ፤ ዛሬ ሰኔ 8 ቀን ከእመቤታችን 33ቱ በዓላት አንዱ ነው፤ ይህም በስደታቸው ወራት ልጇ ከደረቅ አለት ላይ ውኃን ያፈለቀበት ቀን ነው። ይህ ውኃ እንደ ማር እንደ ወተት የጣፈጠ እንደ ወተትም የነጻ ነው፤ ከዚህ ውኃ የጠጣ ሁሉ ይፈወስ ነበር። ታሪኩ እንዲህ ነው የግብጽ በረሃ በጣም ሲያደክማቸው ከአንድ መንደር ያርፋሉ በዚያም ጌታ ውኃ ይጠማዋል ይህን ባየች ጊዜ እምቤታችን ከመንደሩ ሴቶች ውኃ ልትለምን ሄደች፤ ዮሴፍና ሶሎሜ ግን ደከሟቸው ተኝተው ነበር፤ ውኃ የሚሰጣት የሚመጸውታት ስታጣ ልቧ በሐዘን ተወግቶ ተመልሳ መጣች ጌታን ከተቀመጠበት አንስታ ታቀፈችው ስቅስቅ ብላም አለቀሰች ህጻን ጌታም የእናቱን እንባ ከጉንጮቿ ላይ በእጆቹ ጠረገላት ትንሽዬ ጣቱን (ማርያም ጣት የምንለውን ነው ወደ ምድር አመለከተ ወዲያውኑ ጣፋጭ ውኃ ከአለት ላይ ፈልቆ ጠጡ፤ እንዲህም አለ ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ለድህነት ይሁነው ብሎ ባረከው ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሚጠጣው ሁሉ ከደዌው ይፈወስ ነበር፤ አሁንስ ይኖር ይሆን ? እንጃ፤ የጠፋ በግ አዳምን የፈለገው ባገኘውም ጊዜ የተሸከመው እውነተኛ ቸር ጠባቂያችንን የወለድሽልን እመቤቴ ማርያም ሆይ ሠላምታ ይገባሸል የሄዋን ጽኑ የሚጎዳ ማሰሪያዋ ባንቺ የተቆረጠላት እመቤቴ ማርያም ሆይ ውዳሴም ይገባሻል እኛ ከምንወደው እርሱም ከሚወደን ልጅሽ ይቅርታ ያደርግልን ዘንድ ለምኝልን።

LIKE OUR PAGE >>>

Monday, June 9, 2014

እንኳን አደረሳችሁ, ለጦመ ሐዋርያት በሰላምና በጤና አደረሰን:

እንኳን ለጦመ ሐዋርያት በሰላምና በጤና አደረሰን:


LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

በዓለ መንፈስ ቅዱስ/ጰራቅሊጦስ

በዓለ መንፈስ ቅዱስ/ጰራቅሊጦስ

ምንም እንኳን የዕለታትና የዘመናት ሁሉ ባለቤት እርሱ እግዚአብሔር ቢሆንም በእኛ በክርስቲያኖች ዘንድ ነገር ሁሉ በሥርዓት ይሁን ብሎ ሐዋርያው እንዳስተማረን በቤተክርስቲያናችን የበዓላት ሥርዓት መሠረት ከትንሣኤ በኋላ ፶ኛው ቀን በዓለ ጰራቅሊጦስ/በዓለ ሃምሳ/በዓለ ጰንጠቆስጢ ወይንም የቤተክርስቲያን የልደት ቀን በመባል ይታወቃል ወይንም ይከበራል። በግሪክ ቋንቋ ጰራቅሊጦስ ማለት አጽናኝ ማለት ነው።

መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ሥላሴ አንዱ ሲሆን ከአብ የሰረጸ ከአብና ከወልድ ጋር በመለኮት በስልጣን በአገዛዝ በመሳሰሉት እኩል ወይንም አንድ ነው። እንደ እግዚአብሔር አብ እና እንደ እግዚአብሔር ወልድ(ኢየሱስ ክርስቶስ) መንፈስ ቅዱስ በራሱ የተለየ አካልና ግብር አለው። ዮሐ.፲፭፥፳፮። መንፈስ ቅዱስ ከዘመናት አስቀድሞ ከአብና ከወልድ ጋር ዓለማትን የፈጠረ ነው። ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙር ፴፪፥፮ ላይ <በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ጸኑ ሠራዊታቸውም ሁሉ በአፉ እስትንፋስ> ሲል ተናግሯል።

መንፈስ ቅዱስ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር የመጣበትን አላማ አበክሮ የሚገልጽና ጌታችንም ወደ ቀደመ ክብሩ በምስጋናና በእልልታ ካረገ በኋላ በ፲ኛው ቀን ለሐዋርያት ጸጋውን በማፍሰስ የተገለጸ የቤተክርስቲያን ጠባቂና መሪዋ፤ በእግዚአብሔር ልጅ ያመኑትንና በስሙ የተጠሩትን ክርስቲያኖች የሚያጽናና፣ በኃይማኖት በምግባርና በተጋድሎ የሚያጸና፣ ጥበብንና ማስተዋልንም የሚያድል ነው (ኢሣ.፲፩፥ ፪)። ክርስቲያኖች ከጌታ የተማሩትን መልካም የሆነውን የጽድቅ ሥራ እንዲሠሩ ዘወትር በልቦናቸው አድሮ የሚያሳስብ እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው። <አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔ የነገርኳችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል> ዮሐ. ፲፬፥፳፮ በማለት ሐዋርያት/ክርስቲያኖች በሚሠሩት ሥራ ሁሉ መንፈስ ቅዱስ እንደማይለያቸው ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሯል።

መንፈስ ቅዱስ በእምነት ጸንተው በጸሎት ለሚተጉ ክርስቲያኖች ሁሉ የሚሰጥ ኃብት ነው። በተለይም በአንድ ልብ ሆኖ በኅብረት በሚደረግ ጸሎት ምልጃና ጉባዔ መንፈስ ቅዱስ በቶሎ ይሰጣል/ይወርዳል/ይገኛል፤ ለሁሉም እንደ ችሎታውና እንደ አቅሙም ፀጋንና ስጦታን ያድላል። <በዓለ ኀምሳም የተባለው ቀን በደረሰ ጊዜ ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው አብረው ሳሉ፥ ድንገት እንደሚነጥቅ ዓውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ፥ ተቀምጠው የነበረበትንም ቤት ሁሉ ሞላው። እንደ እሳትም የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩአቸው፤ በእያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው። በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው፥ መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደሰጣቸው
በሌላ ልሳኖች ይናገሩ ጀመር> ሐዋ.ሥ. ፪፥ ፩-፬

መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠው ሰዎች መንፈሳዊ ሥራ እንዲሠሩና ሌሎችን ወደ እግዚአብሔር እንዲስቡ እነርሱም በረከትን እንዲቀበሉ ነው። ይህም የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ልዩ ልዩ እነደሆነ ሐዋረያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ እንዲህ በማለት ዘርዝሮታል፦ የጸጋ ስጦታ ልዩ ልዩ ነው መንፈስ ግን አንድ ነው አገልግሎትም ልዩ ልዩ ነው ጌታም አንድ ነው አሠራርም ልዩ ልዩ ነው ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔር ግን አንድ ነው። ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል። ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ ለአንዱም ተአምራትን ማድረግ ለአንዱም ትንቢትን መናገር ለአንዱም መናፍስትን መለየት ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጎም ይሰጠዋል ይህን ሁሉ ግን ያ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል። (፩.ቆሮ.፲፪፥፬-፲፩)

እዚህ ላይ በተለይ በልሳን የመናገር ስጦታ ሲባል ምን ማለት እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል። ልሳን ማለት በአንደበት የሚነገር ትርጉሙንም ቋንቋው ሲነገር የቋንቋው ተናጋሪ የሆኑ ሰዎች ሁሉ የሚረዱት የሰው ልጆች ልሳን/ቋንቋ ነው። አንዳንዶች የተለየ በዚህ ዓለም ያሉ ሰዎች የማይረዱትን ነገር እንደሚያውጡት ያለ ድምጽ እንዳልሆነ መረዳት ይገባል። በዚህ የተታለሉ እኅቶችና ወንድሞች አሉና። ሐዋርያት በልሳን በተናገሩ ጊዜ በዙሪያቸው የነበሩ ከተለያዩ አገሮች የመጡ ሰዎች የእነርሱን ሃገር ልሳን/ቋንቋ ሲናገሩ ሰምተው ተገረሙ ነው የሚለው ቅዱስ ሉቃስ ( ሐዋ.፪ ፥፭-፲፫ )

ለሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ የወረደበት ዋናው ምክንያት ሐዋርያት ዓለምን ዞረው አሕዛብን ሁሉ በየቋንቋቸው በማስተማር የክርስቶስ መንግሥት ተካፋይ እንዲሆኑ ዕድል ፈንታ ይኖራቸው ዘንድ ነው። ሌላው በእምነትና በጽናት ተስፋ ለሚያደርጉት ሁሉ ሳይሳሳ በልግስና የሚሰጥ ቸር አምላክ መሆኑን ሲያስተምረን ነው። በዮሐንስ ወንጌል ፫፥ ፴፬ ላይ <እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና> ተብሎ እንደተጠቀሰው። በተጨማሪም ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያቱ <ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም> ዮሐ.፲፬፥፲፰ ያለውን ቃል ይፈጽም ዘንድ ነው።

መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ወረደ ሲባል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአካል ሥጋ ለብሶ እንደተገለጸው ያለ አገላለጽ ሳይሆን ጸጋውን አደላቸው ማለት ነው። እግዚአብሔር ወልድ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ከደሟ ደምን ከነፍሷ ነፍስን ነስቶ ሰው ሆኖ እግዚአብሔርን አሳይቶናል፤ አይተነዋል። ለዚህም <...እኔን ያየ አብን አይቷል...> ዮሐ.፲፬፥፰ ብሎ በቅዱስ ቃሉ በሕገ ወንጌሉ አስተምሮናል። መንፈስ ቅዱስ ግን የማይታይ የእውነት መንፈስ ነው። የሚታየው/የሚገለጸው በሚያሠራው በጎ ሥራ ነው። ዘወትር በምንሠራው የጽድቅ ሥራ ወይንም በደልና ኃጢአትን በሠራን ጊዜም በውስጣችን ሆኖ ሲወቅሰን መንፈስ ቅዱስ ከኛ ጋር እንዳለ እናውቃለን። <እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለም ከእናንተ ጋር እንዲሆን ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለሆነ ሊቀበለው የማይችለው የእውነት መንፈስ ነው ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሰጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ> ዮሐ.፲፬፥፲፭-፲፯።

መንፈስ ቅዱስ ክርስቲያኖች በድፍረት የኢየሱስ ክርስቶስን ጌትነት እንዲመሰክሩ የሚያደርግ ነው ፩ቆሮ. ም.፲፪፥፫ የኢየሱስ ክርስቶስን ጌትነት መመስከር ሲባልም በዘመናችን እንደምንሰማውና እንደምናስተውለው በብዙ ክሕደት ውሰጥ ሆኖ ኢየሱስ ጌታ ነው ማለት ብቻ ሳይሆን የእርሱን አምላክነት በማመን ጌትነቱ አምላካዊ የሆነና እርሱ ራሱ ምልጃን ተቀባይ እንጂ አማላጅ እንዳልሆነ በማመን መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል። መንፈስ ቅዱስን የተቀበልን ክርስቲያኖችም ዘወትር በተሰጠን ፀጋና ችሎታ ቤተክርስቲያንን፣ ሌሎች ወንድሞችና እኅቶችን፣ ኅዙናንን ማገልገል ባጠቃላይ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ተብለው በሐዋርያው በቅዱስ
ጳውሎስ የተማርነውን ለመፈጸም መትጋት ይኖርብናል። እነዚህ የመንፈስ ፍሬዎች የተባሉትም ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ እምነት፣ የውሃት፣ ራስን መግዛት ናቸው (ገላ.፭፥፳፪-፳፫)። መንፈስ ቅዱስን የተቀበልን ሲባልም በሥርዓተ ቤተክርስቲያን በ፵ እና በ፹ ቀን በጥምቀት የተቀበልነውን ነገር ግን በውስጣችን ተዳፍኖ ያለውን መንፈስ በበጎና በጽድቅ ሥራ መቀስቀስ ማለት ነው ። አንዳንድ የዋሃን እንደሚሉት አዲስ መንፈስ እስኪወርድልን እንደ ሐዋርያት በአንድ ቦታ ተሰብስበን ቤት ዘግተን እንቀመጥ ማለት እንዳልሆነ ልናውቅ ያስፈልጋል። እርሱም የሚያረጋጋና የሚያስደስት እንጅ የሚያስገዝፍና የሚያስጮህ እንዳልሆነ ማስተዋል ይገባናል ።

ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ ሥራውን በኛ ላይ እንዲሠራ በሃይማኖት ጸንተን ራሳችንን ከክፉ ገነር በማቀብ እንድንኖር ያሻል። የያዕቆብ ወንድም ይሁዳም በመልዕክቱ እንዲሁ እንድናደርግ ነው የሚያሳስበን <እናንተ ግን ወዳጆች ሆይ ከሁሉ ይልቅ በተቀደሰ ሃይማኖታችሁ ራሳችሁን ለማነጽ እየተጋችሁ በመንፈስ ቅዱስ እየጸለያችሁ ወደ ዘላለም ሕይወት የሚወስደውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ምሕረት ስትጠባበቁ በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን ጠብቁ> ይሁዳ ፩፥፳። በቤተክርስቲያናቸን ትምህርት መሠረት መንፈስ ቅዱስ የሚወርደው /የወረደው በተለያዩ ምሳሌዎች ነው። በሰው ተመስሎ የተገለጸበት ጊዜ አለ (ዘፍ. ፲፰፥፩) ፣ በርግብ ተመስሎ የወረደበት ጊዜ አለ (ማቴ. ፫፥፲፮)፣ በእሳት የተመሰለበት ጊዜ አለ (ሐዋ.፪፥ ፫፤ ማቴ. ፫፥፲፮)ስለሆነም ዘመናችን ብዙ የሐሰት ትምህርት የሞላበት በተለይም መንፈስ ቅዱስ ወረደልኝ፤ ይወርድልሃል፤ ይወርድልሻል፤ በሚል ማጭበርበርና ማደናገር ብዙዎች ከእውነት የተለዩበት በሐሰት መንፈስ የተወሰዱበት በመሆኑ እውነተኛውን መንፈስ ከሐሰተኛው መንፈስ ለይተን እንድናውቅ ያስፈልጋል። 

በመጨረሻም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ <የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን>ብሎ በ፪ኛ.ቆሮ.፲፫፥፲፬ ላይ አንድ እንሆን ዘንድ በኃይሉ እንዲያበረታን እንደጸለየልን እውነትን አውቀንና ተረድተን ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ያስተማረችንንና የምታስተምረን ተገንዝበን እንድንኖር እርሱ መንፈስ ቅዱስ ይርዳን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር

Source: ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ሰ/ት/ቤ/ት/ክ

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 28

ግንቦት 28 በዚህች ቀን ዓለምን ንቃ የተወች ገዳማዊቷ ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ አረፈች። በበርሃ የሚኖረው አባ ዳንኤል ስለዚህች ሴት እንዲህ አለ፤ ከዕለታት በአንዱ ቀን በጨረቃ ብርሃን በርሃውን አቋርጬ ስጓዝ ተራራ ላይ የተቀመጠ ሰው አየው ግርማው ያስፈራል መላ ሰውነቱን ጸጉር ሸፍኖታል ሰው ይሁን መንፈስ ልረዳ ቀረብኩት እርሱ ግን እንደተመለከተኝ ሮጦ የተሰነ...ጠቀ አለት ውስጥ ገብቶ ተደበቀ፤ ሰው እንደሆነ አወቅኩኝ፤ አባቴ በረከትህን እሻለሁና ወደ ዋሻው አስገባኝ ብዬ ለመንኩት፤ እርሱ ግን ወደኔ መግባት አይቻልህም አለኝ፤ የሴት ድምጽ ነው፤ ለምን አለኳት፤ እርቃኔን ነኝ አለችኝ፤ የለበስኩትን አጽፍ አኖርኩላት እርሱን ለብሳ ወጣች፤ ታሪኳን ሁሉ ነገረችኝ፤ በዘንቢል ሽንብራ በኮዳ ውኃ ይዛ ከወላጆቿ ቤት እንደወጣች ለ 38 ዓመት በኤርትራ በርሃ ሰው ሳታይ ብቻዋን በተጋድሎ እንደኖረች ነገረችኝ እኔም ጻፍኩት ይለናል፤ ይህች ቅድስት እናት ኢትዮጰያዊት እንደሆነች የትውልድ ቦታዋም ሸዋ ውስጥ ተጉለት እንደሆነ በአገራችን አንድ ገዳም እንዳላት ሊቀ ብርሃናት መርቆርዮስ አረጋ "የኢትዮጰያ ተወላጆች ቅዱሳን" በሚል መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል፤ ስንክሳሩም ሰርቶላታል፤ ግንቦት 28 በዛሬዋ ቀን እረፍቷ ነው። በረከቷን ያድለን።

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 26

ግንቦት 26 
በዚህች ዕለት ዲዲሞስ የተባለው ሐዋርያው ቶማሰ አረፈ፤ እርሱም በላይንደኬ በዛሬዋ ህንድ ወንጌልን ሰብኮ ብዙዎችን አሳመነ በዚህም መኮንኑ ተቆጥቶ ጽኑ ስቃይ አሰቃየው ቆዳውንም ገፈፈው፤በሰውነቱም ላይ ጨውና ቆምጣጣ አፈሰሱበት፤ይህንን ሁሉ ታገሰ፤በተገፈፈ ቆዳው ስምንት ሙታን አስነሳ ብዙ ገቢረ ታአምራትን አደረገ፤ይህንን አይተው መኮንኑን ጨምሮ ብዙዎች አመኑ።ከዚህ በኃላ በአቴናና መቄዶንያ ገብቶ ሰበከ ንጉሱም ይዞ አሰቃየው በመጨረሻም በጦር ተወግቶ በዛሬዋ ዕለት በሰማዕትነት አረፈ። የጌታን ጎን የዳሰሰች የሐዋርያው ቀኝ እጅ ተአምራትን እያደረገች እስከ ዛሬ በህንድ አለች፤
በረከቱ ይደርብን

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 24

ግንቦት 24

 በዚህች ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልጇን እግዚያብሔርን ይዛ ከዮሴፍና ከሶሎሜ ጋር ወደ ግብጽ የተሰደዱበት ቀን ነው፤ ይህን ቀን ቤተክርስቲያን በደማቁ አክብራው ትውላለች፤ በመዲናችን አዲስ አበባ እንጦጦ መንበረ ንግስት ቁስቋም ቤተክርስቲያን እንዲሁም ቅዱስ ዮሴፍ ቤተክርስቲያን ታቦተ ሕጉ ወጥቶ በደማቁ ተከብሮ ይውላል። “እነሆ፥ የጌታ መል...አክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ። ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፥ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፥ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው። እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን በሌሊት ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ። ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብፅ ሄደ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ። ማቴ 2፤13 በስደት የቆዩት ሦስት ዓመት ከመንፈቅ ነው የእመቤታችን ስደት ለኢትዮጵያ ታላቅ በረከት ነው የጣና ደሴቶችን የዋልድባ ገዳምን አክሱምና የትግራይ አውራጃዎችን፤ ድብረ ዓባይና የጎጃም ታላላቅ ገዳማትን በርካታ የኢትዮጵያ አውራጃዎችን በኪደተ እገራቸው ባርከውታል ቀድሰውታል።፤ “የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ አለ ነብዩ ዕንባቆም፤ ዕንባቆም 3፤7። ነብዩ ምን ማለቱ ነው ? መቼ ነው የኢትዮጰያ ድንኳኖች የተጨነቁት ? እመቤታችን በስደት ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣም እይደል። ግን ግን ስደቷ ግንቦት 24 ከሆነ ለምን ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 6 ቀን የጽጌ ጾም ብለን ስደቷን እናስባለን ካሉ፤ይህ ሊቃውንቱ የሰሩት ስርዓት ነው፤ ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 25 በቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ ዘመነ ጽጌ ይባላል የአበባ የልምላሜ ወቅት ነው፤ እመቤታችን ደግሞ በአበባ ትመሰላለች አበባ የፍሬ እናት ነው፡፡ እመቤታችንም የተባረከ ፍሬ መድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርሰቶስን ያስገኘች አማናዊቷ አበባ ናት፡ ስለዚህም ይህን የስደቷን ወራት በዘመነ ጽጌ ባሉት 40 ቀናት ከመስከረም 26 እስከ ህዳር 6 ቀን ታስቦ እንዲውል የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ስርዓትን ሰሩ። 
እግርሽ ጨረቃን የሚጫማ 
በአሸዋ ስትሮጪ እግርሽ ደማ
ውቅያኖሶቹ ግራ ቀኙ የሚሰፈሩት በእፍኙ
ለእርሱ ለእርሱ ለዝናብ ጌታ ውኃ ነሱ።
ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>

እንኳን ለጌታችን ለመድሐኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የእርገት በዓል አደረሳችሁ !!!



በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አ፩ዱ አምላክ አሜን

“እያዩት ወደሰማይ ዐረገ”(ሉቃ 24÷50 የሐዋ 1÷9)
ዕርገት

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሞቱ ድል ነሥቶ
የትንሣኤያችን በኩር የሆነው ጌታ በመቃብሩ ቦታ
- ለማርያም መቅደላዊት እና ለሌሎችም ሴቶች (ማቴ 28÷1 የሐዋ 2÷1)፡፡
- ለኤማውስ መንገደኞች( ሉቃ 24÷13)
- ለደቀማዛሙርቱ በተዘጋ ቤት (ዮሐ 20÷8)
- በጥብርያዶስ ባህር ለደቀመዛሙርቱ ዮሐ 21÷4 
ሥርዓትን እያስተማረ አልፎ አልፎም በግልጥ እየታየ ፍርሐታቸውን እያስወገደ አይሁድ እንደሚሉት ሥጋውንም ደቀመዛሙርቱ እንዳልሰረቁት ይልቁንም በሞት ላይ ሥልጣንኑን አሳይቶ መቃብሩን ባዶ አድርጐ በትንሣኤው አለት ላይ ያቆመን፣ ሞት በእርሱ እንደተሸነፈ የማይታየው እየታየ፣ ዘመን የማይቆጠርለት፣ ዘላለማዊ ጌታ የማይዳሰሰው እየተዳሰሰ ለ40 ቀናት ያክል ቆይቶ ተከታዮቹን ሐዋርያትን ወደቢታንያ አወጣቸው፡፡ እያዩት በምስጋና ወደሰማይ ዐረገ፡፡ እንዲህ ተብሎ በነብዩ ዳዊት እንደተፃፈው፡- “ዐረገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለቀርን ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ” እግዚአብሔር በመለከት ድምጽ ዐረገ፣ዘምሩ ለአምላካችን ዘምሩ፣ ዘምሩ ለንጉሣችን ዘምሩ (መዝ 46÷5)

አምላካችን ወደሰማይ ከማረጉ በፊት ደቀመዛሙርቱን ምን አዘዛቸው?

1. ምስክሮቼ ትሆናላችሁ፡፡ (ሉቃ 24÷48) ደቀመዛሙርቱ ያዩትንና የሰሙትን ሞትን አሸንፎ የተነሣውን ጌታ ለዓለም ሁሉ ምስክሮች ሆነዋል፡፡ በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ የዓላውያንን ነገሥታት፣ የቄሳሮችን ዛቻና ማስፈራሪያ አንዳችም ሳይፈሩ ከምድር ዳርቻ እስከምድር ዳርቻ ድረስ ሁሉን እያጡና መከራ እየተቀበሉ፣ እየታሰሩና እየተገረፉ ምስክሮች ሆነዋል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከዚህ በኋላ ስሙን አትጥሩና በስሙም አታስተምሩ እያሏቸው በሸንጐ ፊት ሲያቆሟቸው፣ ሲገርፏቸው ደስ እያላቸው ከሸንጐ ፊት ይወጡ ነበር፡፡ (የሐዋ 5÷40)፡፡ ስለ ስሙ ምስክር መሆን መነቀፍና መታሰር፣ መደብደብ እንዴት ደስ ይላል!፡፡ እኛም እንደ ደቀመዛሙርቱ ማንንም ሳንፈራ አፋችንን ሞልተን ስለ ስሙ እየመሰከርን ሁሉን ብናጣም ሞታችንን በሞቱ ድል የነሣልንን የሚቃወመንን ጠላታችንን በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ያስወገደልንን፣ እረፍትና ሰላም የሰጠንን፣ ጨለማውን ገፎ ብርሐንን ያጐናፀፈንን፣ ያለፈውን ታሪካችንን በነበር ላስቀረልን ምስክሮች እንሁን፡፡

2. አጽናኙን እልክላችኋለሁ (ዮሐ 15÷26)፡-
- በአህዛብና በዓላውያን ነገሥታት ፊት ሲቆሙ እውነትን እንዲናገሩ የሚያፅናና ኃይል፣
- ከተዘጋ ቤት ወደ ሠገነት እንዲቆሙ የሚያደርግ ኃይል፣
- ልበ ሙሉ ሆነው ከጥርጥር ወደ ፍፁም እምነት፣ ከፍርሃት ወደ ድፍረት እንዲሸጋገሩ የሚያበረታታ አጽናኝ ኃይል እልክላችኋለሁ፡፡
ይህ ኃይል በዘመናችን በጣም ስለሚያስፈልገን በፍፁም መዘንጋት የለብንም፡፡ እውነትን ለመናገርና ለመመስከር፣ ፍርሐታችን እንዲወገድልን ከፈለግን ይህንን ኃይል ዓለም ሳይሆን የሚሰጠን ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ መሆኑን አውቀን ጌታ ሆይ እኔን ልጅህ ያንተን ኃይል አጥቼ ደክሜያለሁ፣ ከእኔ የሆነ ኃይል ምንም የለምና ከእኔ አትራቅ፡፡
- ባስልኤልንና ኤልያብን በጥበብ መንፈስ የሞላህ (ዘፀ36÷2)
- ሶምሶንን በጾርዓና በኤሽታኦል ያነቃቃህ (መሳ 14÷18)
- ለደቀመዛሙርቱ ኃይልህን ልከህ 71 ቋንቋ የገለጥክ፣ በየዘመናቱ የተመረጡ አገልጋዮችህ ያፅናናህ፣ የእውነትን ቃል እየላክ ያበረታታህ እኛም እንድንበረታ ኃይልህን ከአርያም ላክልን፣

3. በኢየሩሳሌም ቆዩ (ሉቃ 24÷49)፡- ደቀመዛሙርቱ ከቢታንያ ወደ
ኢየሩሳሌም ተመልሰው በአንድ ልብ ሆነው በኢየሩሳሌም ቀዩ፡፡ በመቆየታቸውም
ሰማያዊ ኃይል አገኙ፡፡
እኛ ሰማያዊ ኃይል ለማግኘት የት እንቆይ?
- በኢየሩሳሌም ቤተክስቲያን መቆየት ያስፈልገናል፣
- በአንድ ልብ ሆነን በቤታችን፣ በአገልግሎታችን፣ በዘር፣ በጐሣ ሳንከፋፈል ይኸ እንዲህ ነው፣ ያ ደግሞ እንዲህ ነው ሳንል ከኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን የወጣንም እንመለስ፣
- ሰዎች ባይመቹንም፣ ክፉዎች ልባችንንን ቢያቆስሉንም፣ ሰዎች እንጂ ያልተመቹን ክርስቶስና ቤተክርስቲያን ሁልጊዜ ይመቹናል፡፡ ስለዚህም ከኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን አንውጣ፡፡ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እየበላንና እየጠጣን፣ እያገለገልን፣ ያደግንባት የእኛ ኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያናችን ብናዝን የምንጽናናባት፣ አእምሮአችን የሚያርፍባት፣ ሰላም የምናገኝባት ኢየሩሳሌም ቤትክርስቷያናችን ናት፡፡

ማጠቃለያ

አምላካችን የማዳን ሥራውን ካጠናቀቀ በኋላ ለተከታዮቹ ደቀመዛሙርት ምስክሮቼ ናችሁ፡፡ አጽናኙን እልክላችኋለሁ፡፡ “አንትሙ ንበሩ በሀገረ ኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ሃይለ እማርያም፡፡ ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ” ብሎ አዘዛቸው፡፡

በመጨረሻም ወደሰማይ ሲያርግ እጆችንም አንስቶ ባረካቸው፡፡ (ሉቃ 24÷51)
በብሉይ ኪዳን ተፅፎ እንደምናገኘው፡- አባታችን አብርሃምን ባርኮ ያበዛ(ዘፍ12÷1)፣ ያዕቆብን በያቦቅ ወንዝ ሲባረክ ያደረ (ዘፍ35÷9)፣ ያቤጽን ባርኮ ሀገሩን ያሰፋ(1ኛ ዜና 4÷9)፣ አምስቱን እንጀራ፣ ሁለቱን ዓሣ አብዝቶ የባረከ ጌታ ዛሬም በኑሯችን አብዝቶ የሚባርከን፣ ሥራችንን እንድንሠራ በበረከት ያጣነውን ደስታ የሚመልስልን፣ ባርኮ በበረከት ወደሚያትረፈርፍልን፣ ጉድለትን ሳይሆን ሙላትን፣ ማጣት ሳይሆን በረከትን ወደሚሰጠን ደቀመዛሙርቱ ዓይኖቻቸውንም ወደላይ ትኩር ብለው እንደተመለከቱት እንደሐዋርያት ማየት ይጠበቅብናል፡፡ እውነት ነው እርሱን ማየት ከሁሉም ይበልጣልና ወደሰማይ ያረገውን ጌታ አይናችንን አንስተን እንይ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 21

ግንቦት 21

ከእመቤታችን 33ቱ በዓላት አንዱ ነው፤በዚህ ቀን ግብጽ ደብረ ምጥማቅ በተባለ ቦታ በተሰራች ቤተክርስቲያን እመቤታችን ጻድቃንን መልአክትን አስከትላ ትገለጽላቸው ነበር፤እስላምም ክርስቲያንም በግልጽ ይመለከቷት ነበር። ከየአገሩ ያሉ ሰዎች ይሰበሰባሉ ድንኳን ተክለው ሰቀላ ሰርተው አጎበር ጥለው ይከትማሉ ፤ድንግልም ከግንቦት 21 ቀን ጀምሮ ለአምስት ተ...ከታታይ ቀናት ሳታቋርጥ ትገለጽላቸው ነበር፤ህዝቡ የተለያየ ጥያቄ ይጠይቃታል አዳም አባታችንን አሳይን ይሏታል ገሚሱ ነብዩ ዳዊትን ገሚሱ ቅዱስ ጊዮርጊስን አሳይን ይሏታል አንዳንዱም ከዚህ ቀደም የሞተ ዘመዱን እንድታሳየው ይጠይቃታል፤እርሷም ለሁሉም ፍቃዳቸውን ትፈጽምላቸው ነበር፤አዳምን ስትጠራው ከሔዋን ጋር ዳዊትን ስትጠራው ከበገናው ጋር ቅዱስ ጊዮርጊስን ስትጠራው ከጸአዳ ፈረሱ ጋር ነው። ወይ ግሩም ታዲያ ይህ በዚያ ደጉ ዘመን ነበር፤አሁን ግን ኃጢያታችን ሲበዛ በረድኤት ካልሆነ በገሃድስ ተገልጻ አትታይም ለበቁ ካልሆነ። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን አባ መርትያኖስ አረፈ፤ ይህም በህጻንነቱ መንኩሶ ለ 67 ዓመት በፍጹም ተጋድሎ የኖረ ነው። ይህ ገድል ትሩፋቱ በሁሉ ዘንድ ተሰማ፤ እነሆ አንዲት በዝሙት ስራዋ እጅግ የምትታወቅ ሴት ዘንድ ወሬው ደረሰ፤ እርሱ እኮ የሴት ፊት ስላላየ ነው እንጂ በፍትዎት ይወድቃል ከክብሩም ይዋረዳል አለቻቸው ባልንጀሮቿም የለም በፍጹም አያደርገውም አሏት፤ እኔ በዝሙት ከጣልኩት ምን ትሰጡኛላችሁ አለቻቸው ብር እንሰጥሻለን አሏት፤በዚህ ተወራርደው ሄደች፤ ሽቶ ተቀባብታ አምራ ተውባ ሄደች፤ስንክሳሩ እጅግ ውብ መልከመልካም ነበረች ይላታል፤ እስኪመሽ ከገዳሙ አቅራቢያ ቆይታ በሩን አንኳኳች የመሸቢኝ እንግዳ ነኝ አሳድረኝ ትለዋለች፤ ነፍሱ ተጨነቀች ባስገባት የዝሙት ጦር ይነሳብኛል ብተዋት እንግዳ ሆኜ መጥቼ መቼ ተቀበላችሁኝ ብሎ ይፈርድቢኛል ደግሞም አውሬ ይበላታል ብሎ አሰበ፤ባስገባት ይሻለኛል ብሎ አስገባት የተቀበችው ሽቶ ዝሙት የሚቀሰቅስ ነው፤ ቀረበችው፤አባቴ በዚህ ማንም አያየንም አብረን እንተኛ አለችው፤እሳት እያነደደ ነበርና እሺ ምን ችግር አለው እዚህ አሳት ላይ ምንጣፍሽን አንጥፊና እንተኛለን አላት፤ አንድም እግሩን ወደ እሳቱ ማገደው ይላል አይንህ ብታሰናክልህ ካንተ አውጥተህ ጣላት አይደል የሚለው መጽሐፉ፤ ደነገጠች ምንድን ነው አባቴ አለችው፤ ይህ ያስደንቅሻልን የገሃነም እሳትን ታዲያ እንዴት ልትችይው ነው አላት እግሩ ስር ወድቃ ይቅር በለኝ አለችው እርሱም ሌሊቱን ሙሉ ሲያስተምራት አደረ፤ ሲነጋ አልተመለሰችም አመንኩሰኝ ከዚህ በኃላ ወደ ዓለም አልመለስም አለችው አመነኮሳት ከደናግል ገዳም ወስዶ ለእመምኔቷ አደራ ሰጣት፤የሚገርመው ይህች እናት ከብቃቷ የተነሳ የመፈወስ ሀብት ተሰጣት ብዙ በሽተኞች ወደርሷ እየመጡ ይፈወሱ ነበር፤ አባ መርትያኖስ ግን ድጋሚ ሌላ ሴት መጥታ እንዳትፈትነው ሰው የማይደርስበት ከባህር መካከል ባለች ደሴት ብቻውን መኖር ጀመረ፤ ከብዙ ዘመን በኃላ መርከብ ተሰብሮ ብዙዎች ሲሞቱ አንዲት ሴት በመርከቡ ስባሪ ተጣብቃ እርሱ ካለበት ደሴት ደረሰች ባያት ጊዜ ደነገጠ አደነቀም ከእርሷ ጋር በአንድነት ስለመኖሩም አዘነ፤ ይምትበላውን ሰጥቷት የምትለብሰውን አዘጋጅቶላት ሲያበቃ ተወርውሮ ወደ ባህሩ ገባ ዓሳ አንበሪም ተሸክሞ ወደ የብስ አደረሰው ከዚህ በኃላ በአንድ ቦታ ላለመቀመጥ ወስኖ በ108 አገሮች የሚገኙ ታላላቅ ገዳሞችን ዞረ በመጨረሻም በዛሬዋ ቀን በክብር አረፈ፤ እመቤታችንን ከሐና ማህጸን ፈጥሮ ከፍጥረተ ዓለም ለይቶ ከሁሉ አልቆ የእናት አማላጅ ትሁናችሁ ብሎ የሰጠን እግዚያብሔር ይመስገን፤ እኛንም ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>

ግነቦት 12

ግነቦት 12 እንኳን ለፍልሰተ አጽሙ ለአበታችን ለአበነ ተክለሀይማኖት አመታዊ ክብረ በአል በሰለም በጤና አደሰን

የአባታቸንና የኢትዮጵያ ፀሀይ የፃድቁ የተክለሀይማኖት ዐፅመ ፍልሰት ክብረ በዓል ግንቦት ፲፪ ከደብረ አሰቦ ወደ ደብረ ሊባኖስ አጽማቸው የፈለሰበት(ፍልሰተ አጽም) በዓለ ንግስናቸው ይከበራል። ይህም ማለት አባታችን 29 ዓመት ቆመው ሲጸልዩ 7ቱን ዓመት ደግሞ ባንድ እግራቸው የጸለዩና አፅማቸው በደብረ አስቦ ከተቀበረበት ወጥቶ አሁን ደብረ ሊባኖስ ገዳም የተሰራበት ቦታ ጋር የፈለሰበት ታላቅ በዓል በተለይ በደብረ ሊባኖስ በታላቅ ሀይማኖታዊ ስርዓት ይከበራል። ካህናት፣መዘምራን ሊቃውንት ሌሊቱን በማህሌት፣ጠዋት በቅዳሴ፣በወረብና፣በዝማሬ፣በስብከት ሊቃነ ጳጳሳት፣መነኮሳት፣ካህናት፣ዲያቆናትና ከዋክብተ ቤተክርስቲያን ምዕመናን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ይከበራል።
የፃድቁ የአባታችን የተክለሀይማኖት በረከት በሁላችን ላይ ይደር፤ አገራችን ኢትዮጵያን ደግሞ ከክፉ ይጠብቃት፤ አሜን!!!

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 11

ግንቦት 11 

በዚህች ቀን የዜማው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ወደ ብሔረ ሕያዋን የተሰወረበት ቀን ነው። ይህ ቅዱስ ከአባ ጌዴዎን ዘመዶች ወገን እርሱም በኢትዮጵያ አገር ከታነጹት አብያተ ክርስቲያናት ለምትቀድም ከአክሱም ካህናት ውስጥ ነው: እርሷም አስቀድሞ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት በውስጥዋ የተከበበ እና አምላክን በወለደች በእመቤታችን በከበረች ድንግል ማርያም ስም የከበረች ናት ::
የዚህ ቅዱስ አባት አዳም የእናቱም ስም ታውክሊያ ሲባሉ :በ512 ዓ ም በአክሱም ከተማ ተወለደ:: እናት እና አባቱም ልጃቸውን ለማስተማር ወደ ዘመዳቸው አባ ጌዴዎን ልከው እንዲማር አደረጉት : ይህም አባት አባ ጌዴዎን ትምህርትን ሊያስተምረው በጀመረ ግዜ መቀበልም ማጥናትም ተሳነው እስከ ብዙ ዘመንም መዝሙረ ዳዊትን ሲማር ኖረ ነገር ግን ከልቡ ማጥናትን እምቢ አለው:መምህሩም አብዝቶ ደበደበው ባሳመመውም ግዜ መታገስ ተሳነው ከአባቶቹ ቤትም ወቶ ዕብነ ሃኪም ወደተቀበረበት ገዳም ሄደ : በውስጡም የወርቅ የብር የልብስ መቀመጫዎች የተመሉ ናቸው: ከአንዲትም ዛፍ አጠገብ ደረሰ ከዚያም አረፈ ትልም ወደ ዛፏ ሲወጣ አየ :ወደ ዛፊቱም እኩሌታ ደርሶ ወደ ምድር ይወድቃል :ሁለተኛም ተመልሶ ወደ ላይ ይወጣል መጀመርያ ወደ ደረሰበት ሲደርስ ይወድቃል:ሲወጣ ሲወድቅ ብዙ ግዜ ያደርጋል : ወደ ሌላ ቦታም አይሄድም 
ከዚህም በኋላ በብዙ ጥረት በብዙ ትጋት በብዙ ድካም በዚያ ከዛፏ ላይ ወጣ:ከዚያችም ከዛፏ ላይ ተቀምጦ በላ :ቅዱስ ያሬድም ወደዚያ ዛፍ ላይ ይወጣ ዘንድ እንደሚተጋ ብዙ ግዜም ከላይ ሳይደርስ ከመካከል እንደሚወድቅ ከዚያም በኋላ በጭንቅ ወደ አሰበው እንደደረሰ የፈለገውንም እንዳገኘ የትሉን ትጋት ባየ ግዜ ሰውነቱን ግርፋቱን እንደምን አትታገሺም ህማሙንስ እንደምን አትችይም አላት መታገስንስ አብዝተሽ ኖሮ ቢሆን እግዚአብሄር በገለጠልሽ ነበር ይንንም ብሎ አለቀሰ ወደ መምህሩ ወደ ጌዲዮን ተመለሰ አባት ሆይ ይቅር በለን እንደቀድሞ ንገረኝ አስተምረኝም አለው:መምህሩ ጌዲዮንም እንዳልከው ይሁን አለው 150ውን መዝሙረ ዳዊት:መሃልየ ነብያትን :መሃልየ መሃልይን :የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ምስጋና ነገረው:81ዱ መጻህፍትን ትርጓሜ የሌሎች መጽሃፍትን ቁትር እና የመሳሰሉትን መጽሃፍተ ሊቃውንት ሁሉ በአንድ ቀን አጥንቶ ፈጸመ::
ከዚህ በኋላ በብዙ ለቅሶ ወደ እግዚአብሄር በለመነ ግዜ ልቡናው ብሩህ ሆኖለት በአጭር ግዜ የብሉይ እና የሃዲስ መጽሃፍትን ተምሮ ፈጸመና ዲቁና ተሾመ:በዚያም ወራት እንደዛሬ በከፍተኛ ቃል የመዝሙር ማህሌት የለም ነበር በትሁት እንጂ :: እግዚአብሄርም መታሰቢያ ሊያቆምለት በወደደ ግዜ ከኤዶም ገነት 3 አእዋፍን ላከለት እነርሱም በሰው አንደበት ተናግረውት ወደ እየሩሳሌም ሰማያዊት ከእነሱ ጋር አወጡት በዚያም 24ቱ ካህናተ ሰማይ የሚያመሰግኑበትን ማህሌት ተማረ::
ወደ አነዋወሩ ወደ ምድርም በተመለሰ ግዜ በአክሱም ዳር ወደ ከበረች ቤተ ክርስቲያን በ3 ሰዓት ገባ በታላቅም ቃል ሃሌ ሉያ ለአብ:ሃሌ ሉያ ለወልድ: ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ :የፅዮንም ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ ዳግመኛም እንዴት እንደሚሰራት የድንኳንን አሰራር ለሙሴ አሳየው አስተማረው አለ:: ይህቺም ምስጋና አርያም ብሎ ጠራት:የቃሉንም ድምጽ በሰሙ ግዜ ንጉሱም ንግስቲቱም ጳጳሱም ከካህናቱ ሁሉ ጋር የመንግስት ታላላቆች እና ህዝቡ ሁሉ ወደ እርሱ ሮጡ:ሲሰሙትም ዋሉ ከዚህም በኋላ ከአመት እስከ አመት በየክፍለ ዘመኑ በክረምት እና በበጋ:በመጸው እና በጸደይ:በአጽዋማት እና በባእላት :በሰንበታትም እንዲሁም በመላእክት በአል በነብያት እና በሃዋርያት በጻድቃን እና በሰማእታት በደናግልም በአል የሚሆን አድርጎ በሶስቱ ዜማው ሰራ :ይህውም ግዕዝ ዕዝል አራራይ ነው::
የሰው ንግግር የአእዋፍ የእንሥሳትና የአራዊት ጩሀት ከነዚህ ከሶስቱ ዜማ አይወጣም :በአንዲት እለትም ቅዱስ ያሬድ ከንጉስ ገበረመስቀል እግር በታች ቆሞ ሲዘምር ንጉሱም የያሬድን ድምጽ እያዳመጠ ልቡ ተመስጦ የብረት ዘንጉን ወይም መቋምያውን በያሬድ እግር ላይ ተከለው ከእርሱም ደምና ውሃ ፈሰሰ ያሬድም መሃሌቱን እስከሚፈጽም አልተሰማውም ነበር ንጉሱም አይቶ ደነገጠ በትሩንም ከእግሩ ላይ ነቀለ ስለፈሰሰው የደምህ ዋጋ የፈለከውን ለምነኝ ብሎ ለያሬድ ተናገረው ያሬድም ላትከለክለኝ ማልልኝ አለው ንጉስም በማለለት ግዜ ወደ ገዳም ሄጄ እመነኩስ ዘንድ አሰናብተኝ አለው ንጉሱም ሰምቶ ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ ተከዘም እንዳይከለክለውም መሃላውን አሰበ እያዘነም አሰናበተው ከዚ በኋላም ቅዱስ ያሬድ ወደ በተክርስቲያን ገብቶ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ ፈጽሞ የከበርሽ እና የተመሰገንሽ ከፍ ከፍ ያልሽ የብርሃን መውጫ የህይወት ማዕረግ የሆንሽ የሚለውን ምስጋና (አንቀጸ ብርሃን) እስከመጨረሻ በተናገረ ግዜ ክንድ ያህል ከምድር ከፍ ከፍ አለ::
ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን ሃገር ሄዶ በጾም በጸሎት ተወስኖ ስጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያ ፈጸመ እግዚአብሄር ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው ከዚ በኋላ ግንቦት 11 ቀን የተሰወረበት ቦታ በሰሜን ጠለምት ደብረ ሐዊ በተባለው ተራራ ነው፤ በዚህ ቦታ በስሙ የታነጸለት አስደናቂ ገዳም አለው፤ በመዲናችን አዲስ አበባም መስቀል ፍላዎር አካባቢ ግሩም ቤተክርስቲያን አለው ዛሬ ታቦተ ህጉ ውጥቶ በደማቁ ተከብሮ. በአንድ ወቅት እመቤ...ታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አባ ሕርያቆስን ከብሕንሳ፤ ቅዱስ ኤፍሬምን ደግሞ ከሶርያ ይዛ ለቅዱስ ያሬድ አክሱም ላይ ተገለጸችለት እንዲህም አለቻቸው በሉ አንተ ቅዳሴዬን አንተ ደግሞ ውዳሴዬን ንገሩትና በዜማ ይድረስው አለቻቸው፤ እነርሱም ነገሩት እርሱም የሚጣፍጥ ዜማ ደረሰ፤ዛሬም ድረስ ጠዋትና ማታ ቤተክርስቲያን ድምጿን ከፍ አድርጋ ይምታሰማው እነዚህ ሶስት ግሩማን አባቶች የተባበሩበትን ምስጋና ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን። የአባታችን የአምሳለ ሱራፌል የሊቁ ማህሌታይ የቅዱስ ያሬድ ጸሎቱ በረከቱ ረድኤቱ በኛ በህዝበ ክርስቲያኑ ላይ በሃገራችን በኢትዮጵያ ላይ ለዘላለም በእውነት ይደርብን !!!!!አሜን

LIKE OUR PAGE >>>

ግንቦት 9


ግንቦት 9 በዚህች ቀን የጌታችን የመድሐኒታችንን የእየሱስ ክርስቶስን መስቀል ያገኘችው እሌኒ ቅድስት አረፈች። ይህችም የታላቁ ንጉስ የቆስጠንጢኖስ እናት ነች። ባለቤቷ ተርቢኖስ ይባላል ነጋዴ ነው ባህር ተሻግረው አገር አቋርጠው ለዓመት ሁለት ዓመት ነግደው ይመለሳሉ ከዕለታት በአንዱ ቀን ወደ አገገራቸው ሲመለሱ መርከብ ላይ ጨዋታ ጀመሩ፤ እኛስ በሠላም ወደ አገራችን ገባን ሚስቶቻችን ግን እንዴት ሆነው ይሆን አሉ ተርቢኖስ ሚስቱን እጅግ ያምናት ነበርና የእኔ ሚስት እንደዚህ ዓይነት ነገር አታውቅም የእናንተ ሚስቶች ያደርጉት ይሆናል እንጂ አላቸው፤ ያንተ ሚስት ከሄዋን ልጆች የተለየች ነችን እኔ ሄጄ ወድጃት ወዳኝ ...ለምጃት ለምዳኝ አፍቅሬት አፍቅራኝ ብመጣ ምን ትቀጣለህ አለው፤ እስከዛሬ የደከምኩበት ወረት ላንተ ይሁን ካልሆነልህ ግን ያንተን እወስዳለሁ አለው፤ በዚህ ተወራርደው ተለያዩ ቤቷ ሄደ አላስገባም አለችው፤ ገረዷን አስጠርቶ ሁለቱ ብቻ የሚተዋወቁበትን እቃ ስጪኝ ወርቅ ብር እሰጥሻለሁ አላት፤ እሺ አንተ ነጋዴዎች መጡ የብስ እረገጡ እያልክ በከተማው ለፍፍ አለችው እንዳለችው በከተማው እየዞረ ለፈፈ፤ ወደ እሌኒ ቅድስት ገብታ እመቤቴ ነጋዴዎች መጡ የብስ እረገጡ እየተባለ ነው ገላሽን ታጠቢ ሽቶም ተቀቢ አለቻት እርሷም ገላዋን ልትታጠብ የአንገት ሐብሏን አስቀምጣ ባኞ ገባች፤ የአንገት ሐብሏ የተርቢኖስ ስም አለበት ወስዳ ሰጠችው፤ እርሱም ሄዶ ‘’እየው ለምጃት ለምዳኝ ወድጃት ወዳኝ መጣሁ ውድ ስጦታም ሰጠችኝ” ብሎ ሐብሉን አሳየው አልተጠራጠረም አመነው የለፋበትን ወረት በሙሉ አስረክቦ እያዘነ ወደ ቤቱ ገባ፤ ምነው ጌታዬ አዝነህ አይሃለሁ ምን ሆንክብኝ አለችው ወረቴን በሙሉ መአበል ወሰደው አላት፤ ታዲያ ለእዚህ ታዝናለህ ያንተም የኔም ዘመዶች ወዳጆች ብዙ ናቸው ተበድረን ትነግዳለህ አለችው፤ እርሱም በአሽሙር ልክ ነሽ ያንቺ ወዳጆች ብዙ ናቸው እኔ ግን ወዳጅ የለኝም ደግሞ በሰጠሁበት አገር ተበድሬ በመጸወትኩበት አገር ለምኜ አልኖርም ወደ ሌላ አገር እሄዳለሁ አላት እኔም ካንተ አልለይም ብላ ተከተለችው በመርከብ ተሳፍረው ሄዱ ከባህሩ መሐከል ሲደርሱ “እሌኒ ሳምንሽ ካድሺኝ ስወድሽ ጠላሺኝ” ብሎ ሐብሉን አውጥቶ አሳያት እኔ አልሰጠሁትም ህያው እግዚያብሔር ምስክሬ ነው አለችው አላመናት ንጹሕ ከሆንሽ ፈጣሪ ያድንሽ ብሎ በሳጥን አድርጎ ከባህር ጣላት ሳጥኑ በቅዱስ ሚካኤል ጣባቂነት እየተንሳፈፈ ባህር ዳርቻ ደረሰ ቆንስጣ የሚባል ንጉስ አገኛት እጅግ መልከመልካም ነበረችና በክብር አገባት ቆስጠንጢኖስንም ወለደችው ቆንስጣ ሲሞት ልጇ ቆስጠንጢኖስ ነገሰ የጌታን መስቀል ለመፈለግ እየሩሳሌም ወረደች መስቀሉንም አገኘች የዚህ ዜና በሰፊው መስከረም 17 የሚተረክ ነው። በ 80 ዓመቷ ጌታችን ተገለጸላት ወዳጄ እሌኒ ቅድስት ወደኔ ልወስድሽ ነው ይላታል ደነገጠች ምነው መኖር ትፈልጊያለሽን ይላታል እንተን እንዳመሰግን ብዬ ነው ትለዋለች ስንት ዓመት ልጨምርልሽ ይላታል ይህማ ባንተ ቸርነት መግባት ይሆንብኝ የለምን ትለዋለች እንግዲያውስ 40 ዓመት ጨምሬልሻለሁ አላት በ 120 ዓመቷ ግንቦት 9 በዛሬዋ ቀን አርፋለች ይህች ቅድስት እናት ያገኘችው ግማደ መስቀል ኢትዮጵያ ውስጥ ይገኛል ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከእሌኒ ቅድስት በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

ግንቦት 7

ግንቦት 7 በዚህች ቀን ታላቁ የቤተክርስቲያን ሊቅ አቡነ አትናቴዎስ አረፈ። ወላጆቹ አረማውያን ነበሩ ያላመኑ ያልተጠመቁ የአባቱ ስም ሐኪም የእናቱ ስም ማርያም ይባላል መስከረም 20 ቀን ነው የተወለደው። አትናቲዎስ ህጻን እያለ የሰፈሩ ልጆች ደስ የሚል ጨዋታ ሲጫወቱ ይመለከታል ለመሆኑ እንዴት ያለ ጨዋታ ነበር ካሉ እንደ ዘመናችን ህጻናት ሌባና ፖሊስ፤ አ...ባሮሽ፤ ኳስ፤ ወይንም እርግጫ… አልነበረም፤ ስርዓተ ቤተክርስቲያን እየሰሩ ነበር የሚጫወቱት፤ እትናቴዎስ እኔንም ከጫወታችሁ አስገቡኝ አላቸው እነሱም አንተ ያልተጠመቅህ አረማዊ ነህ ከጫወታችን አትገባም አሉት እሺ አጥምቁኝና አስገቡኝ ሲላቸው የጫወታ ጥምቀት አጠመቁት የጫወታ ሊቀ ጳጳስ አድርገው ሾሙትና ወንበር ላይ አስቀመጡት ሰገዱለት ፤ በዚያን ወራት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ የነበረው እለእስክንድሮስ ነው ደቀመዛሙርቱን አስከትሎ መንገድ ሲሄድ የእነዚህ ህጻናትን ጫወታ በመገረም ቆሞ ተመለከተ፤አባታችን ከነዚህ ህጻናት ምን ቁም ነገር ይገኛል ብለህ ትመለከታቸዋልህ አሉት፤እርሱም ይገኛል እንጂ ልጆቼ እነዚህ ህጻናት ያደረጉት በኃለኛው ዘመን እግዚያብሔር በእኔ ላይ አድሮ የሚሰራው ስርዓት ነው፤እነሆ በግብጽ ምድር ጽኑ ርሀብ ይከሰታል የዚህ ህጻን አባቱ ይሞታል እናቱም እንዳሳድገው አምጥታ ለእኔ ትሰጠኛለች ከእኔ በኃላ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ የሚሆነው ይህ ህጻን ነው ብሎ ትንቢት ተናገረለት፤ እንዳለውም ሆነ አባቱ ሲሞት እናቱ ቢኖርም ቢሞትም ከዚህ በኃላ አባቱ አንተ ነህ ብላ አደራ ሰጠችው፤እርሱም በመልካም ስነ ምግባር አሳደገው ዲቁና ቅስና ሾመው በኃላም እርሱ ሲሞት 20ኛው የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ እድርገው ሾመውታል፤ በዚህ በሹመቱ ወራት ብዙ ድርሳናትን ተግሳጻትን መልዕክታትን ጽፏል፤ ግሩም ቅዳሴም ደርሷል፤ እንዲያውም በዛሬዋ ቀን አብዛኞቹ አብያተክርስቲያናት ቅዳሴ እትናቴዎስን ነው የሚቀደሰው፤ እንዴት ያለ ግሩም ቅዳሴ ነው/// በነገራችን ላይ አቡነ አትናቴዎስ የመጀመሪያውን የኢትዮጰያን ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃንን ቀብቶ የሾመ አባት ነው፤ይህ ታሪክ ደግሞ በሁለተኛ ደረጃና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ደረጃ የታሪክ ትምህርት ካሪኩለም ውስጥ የተካተተ ነው። አቡነ አትናቴዎስ 318ቱ ሊቃውን በኒቂያ ጉባዬ አርዮስን ተከራክረው ሲረቱ አፈጉባዬ የነበረ አባት ነው፤ ልክ እንደ ዲዮስቆሮስ በደሴተ ጋግራን ለሰባት ዓመት በግዞት ኖሯል፤ይህን አባት የማይጠቅሰው ሊቅ የለም፤ ሃይማኖተ አበው ላይ በስፋት ይገኛል፤ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ለ 46 ዓመት ህዝቡን በፍቅር ካገለገለ በኃላ ግንቦት 7 ቀን በክብር አርፏል፤ በረከቱ ይደርብን።

LIKE OUR PAGE >>>
https://www.facebook.com/pages/ተዋህዶ-ሀይማኖታችን/117298008428339?ref=hl

ልደታ ለማርያም


ጴጥርቃ እና ቴክታ የሚባሉ ሰዎች በኢየሩሳሌም በአንድነት ተጋብተው ይኖሩ ነበር:እነዚህም በእግዚአብሄር የሚያምኑ የተወደዱ ጻድቃን ደግ ሰዎች ነበሩ:እነዚህም ሰዎች በእግዚአብሄርም በሰውም ዘንድ የበቁ ባለጸጎች ነበሩ:ነገር ግን የሚወርሳቸው ልጅ አልነበራቸውምና መካን ነበሩ:አንድ ቀን ጴጥርቃም ቴክታን እህቴ ሆይ ይህን ሁሉ የሰበሰብነውን ገንዘባችንን ምን እናደርገዋለን ልጅ የለን የሚወርሰን:አንቺም መካን ነሽ እኔም ካንቺ በቀር ሌላ ሴት አላውቅም አላት:እርሱአም ወንድሜ ሆይ አምላከ እስራኤል ለኔ ልጅ ቢነሳኝ አንተም እንደኔው ሆነህ ትቀራለህን? ከሌላ ደርሰህ ውለድ እንጂ ብላ ብታሰናብተው እንደዚ ያለ ነገር እንኩአንስ ላደርገው በልቦናዬ እንዳላስበው አምላከ እስራኤል ያውቅብኛል አላት:እሱአም አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን የሚያውቅ የለም:ትላንትና ማታ በህልሜ ነጭ ጥጃ ከማህጸኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ሌላ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንዲሁ እስከ 7ት ትውልድ ሲዋለድ ሰባተኛይቱ ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋም ፀሃይን ስትወልድ አየሁ አለችው::
እርሱም በጠዋት ከህልም ፈቺ ዘንድ ሂዶ የነገረችውን ሁሉ ነገረው:ያም ህልም ፈቺ እግዚአብሄር በምህረቱ አይቱአቹአል በሳህሉ መግቡአችሁአል 7 አንስት ጥጆች መውለዳቹ 7 ሴቶች ልጆች እና የልጅ ልጆች ትወልዳላቹ ከቤታቹ ሰባተኛይቱ ጨረቃ መውለዱአ ከሰው የበለጠች ከመላእክትም የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹ የፀሃይ ነገር ግን አልታወቀኝም አለው:እርሱም የነገረውን ሁሉ ሄዶ ነገራት እርሱአም እንጃ አምላከ እስራኤል የሚያደርገውን ማን ያውቃል ብላ ዝም አለች:ከዛም ፀንሳ በ9 ወሩአ ሴት ልጅ ወለደች:ስሙአንም ሄሜን ብለው አወጡላት:ሄሜንም አድጋ ለአካለ መጠን ስደርስ አጋብተዋት ሴት ልጅ ወለደች በስምንተኛ ቀኑአም ደርዲ ብለው ስም አወጡላት:ደርዲም አድጋ እንዲሁ ሴት ወለደች እና ቶና አለቻት:ቶናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሲካር አለቻት;ሲካርም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሴትና አለቻት:ሴትናም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ሄርሜላ አለቻት:ሄርሜላም እንዲሁ ሴት ልጅ ወልዳ ንጽህት ቅድስት ክብርት የምትሆን እመቤታችንን የምትወልደውን ሃናን ወለደች::
ከጴጥርቃና ከቴክታ የተወለዱ 67 ወንዶች ልጆች አሉ የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ትውልድ ለመቁጠር ትንቢት አልተነገረላቸውም ሱባኤ አልተቆተረላቸውምና አልተፃፈም:ይህቺም ሃና በስራት በቅጣት አደገች:ለአእምሮ ስትበቃ አካለ መጠን ስደርስ ከቤተ መንግስት ወገን ከነቅዱስ ዳዊት ወገን ከሆነው(መጽሃፍ ቅዱስ ይገልጸዋል) ከቅዱስ እያቄም ጋር አጋቡአት::እነዚህ ቅዱሳን እያቄም እና ሃና በአንድነት ተጋብተው ሲኖሩ ልጅ አጡ:ከእለታት አንድ ቀን ወደ ቤተ እግዚአብሄር ሂደው ሲፀልዩ ሲያዝኑ ዋሉ:ሃዘናቸው እንዴትስ ነው ቢሉ:እያቄም:-"አቤቱ ጌታዬ ያባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለው አትጣለኝ:አትናቀኝ:ፀሎተን ስማኝ ፈቃዴን ፈጽምልኝ:ለአይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የሚሆን የተባረከ ወንድ ልጅ ስጠኝ" ብሎ ሲለምን ዋለ:ሃናም በበኩሉአ "አቤቱ ጌታዬ የአባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለው:ስማኝ ለአይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የምትሆነኝ የተባረከች ሴት ልጅ የማህፀኔን ፍሬ ስጠኝ" ብላ ስትለምን ዋለች: እንዲ ብለው ስይዝኑ ሲጸልዩ ውለው ርግብ ከልጆቹአ ጋር ስትጫወት አይታ አቤቱ ጌታዬ ለዚች ግእዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኅኝ ብላ ምርር ብላ አለቀሰች:እንዲ ብለው ሲያዝኑ ሲፀልዩ ውለው ከዘካርያስ ከሊቀ ካህናቱ ሄደው አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሄርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን:ሴት ልጅም ብንወልድ ማይ ቀድታ መሶብ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን ብለው ስለት ገቡ::
ዘካርያስም እግዚአብሄር ጸሎታችሁን ይስማላቹ ስእለታችሁን ይቀበልላቹ ጻህቀ ልቦናችሁን ይፈጽምላቹ ብሎ አሳረገላቸው:
ከዚያም በሁአላ ቅድስት ሃና እና ቅዱስ እያቄም እለቱን ራእይ አይተው ነገር አግንተው አደሩ:ራእዩም እንዴት ነው ቢሉ ኢያቄም 7ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ አላት:ወፍ የተባለው ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው:ነጭነቱ ንጽሃ ባህሪው ነው:ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ማለቱ:የኢያቄምን ባህርይ ባህርይ እንዳደረገው እወቅ ሲል ነው:7ቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ልዩ ባህሪው:ምልአቱ:ስፍሃቱ:ርቀቱ:ልእልናው:ዕበዩ መንግስቱ ናቸው:ሃናም እኔም አየሁ አለችው:ምን አየሽ ቢላት:ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ አለችው::ርግብ የተባለች እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት:ነጭነቱአ ንጽህናዋ:ቅድስናዋ ድንግልናዋ ነው:ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማህጸኔ ስትተኛ አየሁ ማለቱአ ብስራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችንን መፀነሱአ ነው:ይህንኑም ራእይ ያዩት ሃምሌ 30 ዕለት ነው::
እነሱም እንዲ ያለ ራዕይ ካየን:ነገር ካገኘን ብለው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም:ፈቃደ እግዚአብሄር ቢሆን ብለው አዳምንና ሄዋንን ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት ብሎ ያበሰረ አምላክ ለኛስ ይልክልን የለምን? ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ 7 ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ:ነሃሴ በባተ በሰባተኛው ቀን ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ዓለሙ ሁሉ ተሰብስቦ ቢመዘን አንድ የራሱአን ፀጉር የማያህል ደግ ፍጥረት ትወልዳላቹህና ዛሬ በሩካቤ ስጋ ተገናኙ ብሎአቹሃል ጌታ ብሎ መልአኩ ለሃና ነገራት በፈቃደ እግዚአብሄር በብስራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም እሁድ እለት ተፀነሰች(በኦሪት ስርአት እሁድ ዕለት ባል እና ሚስት መገናኘት ልማድ ነበርና):እመቤታችን የተፀነሰች ዕለት አይሁድ ቀንተው ተነሱባቸው ቅናቱ እንዴት ነው ቢሉ:ሳሚናስ የሚባል የጦሊቅ ልጅ ከኤዶቅ ካጎቱ ቤት ሄዶ ሞተ እነርሱም እንቀብራለን ብለው ባልጋ ይዘው ሲሄዱ ከመንገድ አሳረፉት:የሃናም የአጎቱአ ልጅ ነበርና ለማልቀስ ብትደርስ ዘመዶቹአ ሁሉ ተሰብስበው ሲላቀሱ ቆዩአት:እርሱአም አብራ እየዞረች ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ብድግ ብሎ ተነስቶ ስብሃት ለኪ ማርያም እሙ ለፀሃየ ጽድቅ ለአብ ሙሽራው ለወልድ ወላዲቱ ለመንፈስቅዱስ ጽርሃ ቤቱ ተፈስሂ ደስ ይበልሽ ብሎ ሰገደላት:አይሁድ ከዛ ነበሩና ምነው ሳሚናስ ምን አየህ? ምን ትላለህ? ቢሉት ከዚች ከሃና ማህፀን የምትወለደው ህፃን ሰማይ ምድርን:እመቅ አየርን የፈጠረ አምላክን ትወልዳለች እያሉ መላእክት ሁሉ ሲያመሰግኑአት ሰማሁአቸው እኔንም ያነሳችኝ የፈወሰችኝ ያዳነችኝ እርሱአ ናት አላቸው በል ተወው ሰማንህ ብለው ቅናት ጀመሩ::
""እመቤታችን እግዝትእነ ማርያም በተፀነሰች በ9 ወር ከአምስት ቀን የግንቦት መባቻ ዕለት ግንቦት 1 ተወለደች::""
እመቤታችን እግዝትእነ ማርያም የተወለደችበት እለት በአባት እናቱአ ቤት ፍስሃ ደስታ ተደረገበት ቤቱንም ብርሃን መላው በስምንተኛውም ቀን ""ማርያም"" ብለው አወጡላት::ስለምን ማርያም ብለው አወጡላት ቢሉ:እነሆ በዚ አለም ከሚመገቡት ሁሉ ምግብ ለአፍ የሚጥም ለልብ የሚመጥን "ማር" ነው:በገነትም በህይወት የተዘጋጁ ጻድቃን ቅዱሳን "ያም" የሚባል ምግብ አላቸው ::ከዚ ሁሉ የበለጥሽ የከበርሽ ነሽ ሲሉ ስለዚህ "ማርያም" ብለው አወጡላት::የእመቤታችን ማርያም ስም ተነቦ ሳይተረጎም ይቀር ዘንድ አይገባምና:-""ማ"" ማለት ማህደረ መለኮት: ""ር"" ማለት ርግብየ ይቤላ: ""ያ"" ማለት ያንቀዓዱ ኃቤኪ ኩሉ ፍጥረት:""ም"" ማለት ምስሃል ወምስጋድ ወምስትሥራየ ኃጥያት ማለት ነው::አንድም "ማርያም" ማለት ልዩ ከጣዖት:ክብርት እምፍጥረታት:ንጽህት እምሃጥያት:መልክ ከደም ግባት የተሰጣት ማለት ነው:ዳግመኛም "ማርያም" ማለት ተፈስሂ ቤተ ይሁዳ ወተሃሠዪ ቤተ እስራኤል ማለት ነው::
አንድም "ማርያም" ማለት መርህ ለመንግስተ ሰማያት ማለት ነው:ይህስ እንዴት ነው ቢሉ:እነሆ ዛሬ በዚህ አለም ለዕውር መሪ በትር እንዲሰጡት ሁሉ እርሱአም በፍቅሩአ:በጣዕመ ፍቅሩአ የሰውን ሁሉ ኃጥያት:ክፋት ፍቃ ከልጁአ ከወዳጁአ አስታርቃ ከገሃነመ እሳት አውጥታ መንግስተ ሰማያት የምታስገባ ስለሆነች ስለዚህ መርህ ለመንግስተ ሰማያት አሉአት::አንድም ማርያም ማለት ሰረገላ ፀሃይ ማለት ነው:አንድም ማርያም ማለት ተላኪተ እግዚአብሄር ወሰብእ ማለት ነው:አንድም ማርያም ማለት ውብህት(ስጥውት) ማለት ነው::
በግንቦት አንድ ቀን እመቤታችን አለምን ልታስምር ከቅድስት ሃና እና ከቅዱስ እያቄም በብዙ ልመና ተገኘች:: 
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅሩአ ጣዕሙአ በረከቱአ ረድኤቱአ አማላጅነቱአ በእውነት በኛ አማላጅነቱአን በምናምን ልጆቹአ ላይ ይደርብን::

https://www.facebook.com/photo.php?fbid=292837507541054&set=a.117306178427522.24396.117298008428339&type=1&theater

LIKE OUR PAGE >>>

ትንሳኤ ክርስቶስ


ትንሳኤ ማለት ተንሥአ ካለው የግዕዝ ግሥ የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙም መነሣት አነሣሥ ማለት ነው ።እስራኤል ዘስጋ ያከብሩት የነበረው በዓለ ፋሲካ ከባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት ከኀዘን ወደ ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነበር ።
የሐዲስ ኪዳን በዓለ ትንሣኤ ግን እሥራኤል ዘነፍስ ወደ ከኃጢአት ጽድቅ የተመለስንበት ከሐሳር ወደ ክብር ከአሮጌው ወደ ሐዲስ ሕይወት የተሸጋገርንበት መንፈሳዊ የነጻነትበዓል ነው ።ፋሲካ በዐረብኛ ፓስኻ ማለት ሲሆን ትርጉሙም ማዕዶት መሸጋገሪያ ማለትነው ።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ በቀደምት ነቢያት የተነገሩና የተጻፉ አንቀጾች ብዙ ናቸው፡፡ የሞቱና የትንሣኤ ምሥጢር በቅዱሳን መጻሕፍት ሰፊ ቦታ ያለው ነው፡፡ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚነገረው ሞትና ትንሣኤ ከቅርቡ /ከመስቀሉ አካባቢ/ በመነሣት እሱ ራሱ መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥርዓተ ቊርባንን በሠራበት ምሽት የሞቱንና ትንሣኤውን ነገር አንሥቶ ለደቀ መዛሙርቱ በሰፊው ገልጿል፡፡ “በዚች ሌሊት ሁላችሁ ትክዱኛለችሁ መጽሐፍ እረኛው ይመታል የመንጋው በጎች ይበተናሉ ያለው ይፈጸማል” ብሎ ነግሮአቸዋል፡፡ ከዚህም ቀደም ብሎ በጉባኤው ይሰበሰብ ለነበረው ሕዝብ ዮናስ በከርሠ አንበሪ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት እንደኖረ ወልደ እጓለ እመሕያው ክርስቶስም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ያድራል፡፡ ነገር ግን ወደገሊላ እቀድማችኋለሁ እያለ ይነግራቸው፥ ያስተምራቸው ነበር፡፡ ማቴ ፲፪፥፵፣ ፳፯፥፴፩

መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሱ በተጻፈው መሠረት የመስቀልን ፀዋትወ መከራ ተቀብሎ በመስቀል ላይ ሞቶ፥ ሞትን ይሽረው ዘንድ ሙታንን በሞቱ ሕያዋን ያደርጋቸው ዘንድ ሞተ፡፡ በዕለተ ዓርብ የፈጠረውን አዳም በፈጸመው በደል ከተፈረደበት የሞት ፍርድ ነፃ ይሆን ዘንድ፥ በባሕርዩ ሞት የሌለበት አምላክ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ ዋለ፡፡ ወዳጆቹ የአርማትያሱ ዮሴፍና፥ አስቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታ የሄደው ኒቆዲሞስ በመስቀል ላይ የዋለውን ሥጋውን አውርደው፥ ለመቅበር፤ ከገዥው ከጲላጦስ ለምነው እንዲቀብሩ ተፈቅደላቸው፡፡ ከምሽትም ከመስቀሉ አወረዱት እንደቤተ አይሁድ የአቀባበር ሥርዓትና ልማድ የደቀቀና መዓዛው የጣፈጠ ሽቱ አዘጋጅተው፥ ከጥሩ ሐር በተሠራ በፍታ ገንዘው ዮሴፍ ለራሱ አስወቅሮ ባሳነፀው አዲስ መቃብር ቀበሩት፡፡ታላቅ ድንጋይም አገላብጠው ገጠሙት ማቴ ፳፯፥፶፯‐፶፰፣ ዮሐ፲፱፥፴፰‐፵፪ ይህ ሁሉ ለአይሁድ ሊቃናትና ሕዝብ ደስ የሚያሰኝ አልበረም፡፡ ስለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚደረገው ጥንቃቄና የሚሰጠው ክብር ሁሉ፥ በነሱ ዘንድ ተቀባይነት አልነበረውም፡፡ 
“ያ በሕይወተ ሥጋ ሳለ በሦስተኛው ቀን እነሣለሁ ብሏልና ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት ሰርቀው፥ ወስደው ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ብለው ሕዝቡን እንዳያስቱ መቃብሩ ይጠበቅ” በማለት ወስነው ነበር፡፡ በእያንዳንዱ አራት አባል የሚገኝበት በሦስት ፈረቃ የሚጠብቅ የጭፍራ ቡድን ተመድቦ መቃብሩን በንቃትና በጥንቃቄ እንዲጠብቅ ተደርጓል፡፡ ባለሥልጣኖችም ጭፍራው ባለበት መቃብሩን አስቆልፈው በየቀለበታቸው (ማኅተማቸው) አትመውት ነበር፡፡ ማቴ ፳፯፥፷፪-፷፮
ይህ ሁሉ በሚፈጸምበት ዕለትና ጊዜ እነማርያም መግደላዊት፣ ማርያም ባወፍልያና እና ሰሎሜ ከእግረ መስቀሉ ሳይለዩ ከመቃብሩ ፊት ለፊት ቆመው በኀዘን፣ በተሰበረ መንፈስ የነገሩን ፍጻሜ የሚመለከቱ የዓይን ምስክሮች ነበሩ፡፡ ማቴ ፳፯፥፷፩ ይሁን እንጂ ሰውን ለመዳን በፈቃዱ ባደረገው የቸርነት ሥራ፥ በሥጋ ቢሞትም በባሕርዩ ሞት የሌለበትን ጌታ ሞትና መቃብር ይዘው ሊያስቀሩት የማይቻላቸው በመሆኑ፤ ኃጢአትን፣ ሞትንና መቃብርን ደምስሶ፥ መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ፣ ሳይል በሦስተኛው ቀን በሌሊተ እሑድ ከሞት ተነሥቷል፡፡ በመቃብሩ ላይ ተገጥሞ የነበረው ታላቅ ድንጋይ ተገለባብጦ የተጠቀለለበት የከፈን ጨርቅ በአፈ መቃብሩ ተቀምጦ ተገኝቷል፡፡ የአይሁድ ጎመድ ሁሉ አልነበረም፡፡ ለጥበቃ ተመርጠው ልዩ መመሪያና ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶአቸው የነበሩ ጭፍሮችም ራሳቸውን እንኳ መጠበቅ ተስኗአቸው በያሉበት ወድቀው እንደ በድን ሆነው ነበር፡፡ ትንሣኤውን ለማየት ወደ መቃብሩ ሲመላለሱ ያነጉት ቅዱሳት አንስት ከሞት የተነሣውን ክርስቶስን ለማየት ቀዳሚ ዕድል ነበራቸው፡፡ አስቀድማ ለማየት የበቃችው ማርያም መግደላዊት መሆኗን ቅዱስ ወንጌል አስቀምጦታል፡፡ ከሷ በማስከተል፥ ሁሉም ሴቶች አይተዋል፡፡ 
ጌታችን በተነሣ ጊዜ፥ መልአኩ እንደ ፀሐይ በሚያበራ ልብስ እንደ በረዶ በነጣ ግርማ ርእየቱ በሚያሰፈራ ሁኔታ ተገልጦ ነበር፡፡ ሴቶቹንም “አይዞአችሁ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ ዐውቃለሁ፤ እሱ ከዚህ የለም እንሣለሁ እንዳለ ተነሥቷል፡፡ ነገር ግን ኑ የተቀበረበትን ቦታ እዩ ካያችሁም በኋላ ፈጥናችሁ ሄዳችሁ ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው በገሊላ ይቀድማች ኋል (መታየትን ይጀምርላችኋል) በገሊላ ታዩታላችሁ” ብሎአቸው፥ ወደ መቃብሩ እየመራ ወሰዳቸው፡፡ ሴቶችም ፍርሃትና ድንጋጤ በተቀላቀለበት የደስታ መንፈስ ተውጠው ወደ መቃብሩ ሄዱ፡፡ ፍርሃት የእግዚአብሔርን መልአክ ማየታቸው፤ ደስታው ደግሞ፥ ትንሣኤውን መስማታቸው ነው፡፡ በደስታ ተሞልተው ዜናውን ለደቀ መዛሙርቱ ነግረው፥ እየተቻኮሉ ሲሄዱ ጌታችንን በመንገድ ተገለጠላቸው፡፡ 

“እንዴት ሰነበታችሁ! አስታረቅኋችሁ” አላቸው፡፡ ቀርበውም ሰገዱለት፤ እሱም አይዞአችሁ አትፍሩ፤ ሂዱ ለወንድሞቻችሁ ገሊላ ይሂዱ ዘንድ ንገሩአቸው በዚያ ያዩኛል” አላቸው፡፡ ዐሥራ አንዱ ሐዋርያትም ዜናውን ሰምተው ወደተባሉበት ቦታ ወደ ገሊላ ሄዱ፡፡ በዚያም ጌታችንን ከሙታን ተነሥቶ አዩት፤ ሰገዱለትም፡፡ ማቴ ፳፰፣ ማር ፲፮፡፩‐፲፪፣ ሉቃ ፳፥፲፪ ለፍቅሩ ይሳሱ፥ ይናደዱ የነበሩ ጴጥሮስና ዮሐንሰም በጊዜው ወደ መቃብሩ ሄደው መነሣቱን አረጋገጡ፡፡ ዮሐ፳፥፩‐፲፩፣ ፲፰

የክርስቶስ ትንሣኤ በስሙ ላመኑ ክርስቲያኖች ሁሉ ትንሣኤ ነው፡፡ ክርስቶስ ለሙታን ሁሉ በኲር ሆኖ ተነሥቶአል፡፡ የሙታንን ሁሉ መነሣት የሚያረጋግጥልን የጌታ ትንሣኤ ነው፡፡ የክርስቶስም ትንሣኤ መርገመ ሥጋ፥ መርገመ ነፍስ፤ ሞተ ሥጋ፥ ሞተ ነፍስ የተሻረበት ርደተ ገሃነም ጠፍቶ፥ በአዳም የተፈረደው ፍርድ ሁሉ ተደምስሶ፤ ፍጹም ነፃነት፣ የማይለወጥ ደስታ፣ የተገኝበት ስለሆነ ፋሲካ ይባላል፡፡ ፋሲካ ደስታ ነው እስራኤል ከግብጽ ባርነት ነፃ የወጡበትን ቀን ፋሲካ ብለውታል፡፡ የእርቅ፣ የሰላም፣ የድኅነት ቀን ነው ከሞት ከመነሣት ከመቃብር ጨለማ ከመውጣት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ከመላቀቅ፥ ከሲኦል እስራት ከመፈታት የሚበልጥ ምን ደስታ ሊኖር ይችላል?
የክርስቶስ ትንሣኤ እግዚአብሔር እኛን ምን ያህል እንደ ወደደን የምናስተውልበት፣ የፍቅሩን ጥልቀት፤ የቸርነቱን ስፋት የምናደንቅበት፤ የነፍሳችን የዕረፍት ቀን ነው፡፡ በሰው ዘንድ በቃል ሲነገር በተግባር ሲፈጸም የሚታየው ፍቅር ዘመድ ወዳጅ የሚለይበት ሰው ከሰው የሚዳላበት፤ ባለ ካባ ከባለ ካባ፣ ባለዳባ ከበለዳባ የሚበልጥበት፤ የሚወደውን የሚወዱበት፤ የሚጠላውን የሚጠሉበት ነው፡፡ ለሚጠሉት ይቅርና ለሚወዱት ተላልፎ የሚሞቱበት ፍጹም ፍቅር በዓለማችን አይታይም፡፡ 
መድኃኔዓለም ክርስቶስ እኛን የወደደበት ሕይወቱን እስከመስጠት ደርሶ ቤዛ የሆነበትን ምሥጢር የሰው ሕሊና መርምሮ ሊደርስበት የሚችል አይደለም፡፡ ተነጻጻሪ ተወዳዳሪ አቻ ምስያ የሌለው ልዩ ነው፡፡ ከቀደምት አበው እነ አብርሃም ልጆቻቸውን በቁርጥ ሕሊና ለመሥዋዕት አቅርበዋል፡፡ እነ ሙሴ እነ ዳዊት ይመሩት ይጠብቁት ለነበረው ሕዝብ ተላልፈን እንሙት እንቀጣ የሕዝቡን ቅጣት እንቀበል ብለው እንደነበረ ተጽፎአል፡፡ ግን በቅርብ ለነበረ፣እንዲያስተዳድሩ ለተሾሙለት ለተወሰነ ሕዝብና ለወገናቸው ብቻ ነበር፡፡ ሁሉን የሚያጠቃልል ሁሉን የሚያድን አልነበረም፡፡ 

መድኃኒታችንን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በመስቀል ላይ መከራ ተቀብሎ የሞተው፥ ለመላው የሰው ዘር ለአዳም ልጆች ሁሉ ነው፡፡ ቤተሰብና ዘመድ ወዳጅና ጠላት ወንዝና አካባቢ የሚለው አልነበረም፡፡ ከሰው አስተሳሰብ ሚዛንና ግምት የራቀ የጠለቀ ነው፡፡ የወደደን መከራ የተቀበለው እኛ ስለወደድነው አልነበረም፡፡ እሱ ስለ ወደደን ብቻ ነው፡፡ ስንኳንስ ቀድሞ ዛሬም ያደረገልንንና ያደለንን አስበን፥ ፍቅሩን ተገንዝበን፥ ለሰው በጎ ማድረግ፤ በፍቅሩ መመላለስ እጅግ ያዳግተናል፡፡ ከሁሉም የሚረቀውና የሚደንቀው ያጠፋን የበደልን፣ በጥፋታችን ሞትን በራሳችን ላይ ያመጣን እኛ ስንሆን፥ እሱ ስለኛ በደል ተላልፎ በእኛ የተፈረደውን የሞት ፍርድ ተቀብሎ መሞቱ ይደነቃል፡፡ ለዚህም አንክሮ ይገባል፡፡ 
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ርእዩ መጠነ ዘአፍቀረነ እግዚአብ ሔር … ወሶበ እንዘ ፀሩ ንሕነ ተሣሃለነ በሞተ ወልዱ እግዚአ ብሔር ምን ያህል እንደወደደን አስተውሉ ጠላቶቹ ስንሆን በልጁ ሞት ይቅር አለን” ብሎ እንዳስተማረው ስንኳን ተላልፎ እስከመሞት የሚያደርስ ፍቅርና ከፍርድ የሚያድን ምንም መልካም ሥራ ሳይኖረን፤ በሱ ፍቅር የተደረገልንን ቸርነት የምናስብበት የነፃነት የምስጋና ዕለት ነው፡፡ ሮሜ ፭፥፮‐፲በልጁ ሞት ስለካሰልን ይቅርታን አገኝን፤ በአንድ አዳም በደል ምክንያት ኃጢኣት ወደ ዓለም እንደ መጣች፤ በዚችም ኃጢኣት ምክንያት፥ በሰው ሁሉ ሞት እንደተፈረደበት፤ ሰውን ሁሉ በደለኛ፣ ኃጢአተኛ፣ አሰኝቸው፡፡ በአዳም ኃጢአት ምክንያት የመጣ ሞት ከአዳም እስከ ክርስቶስ የነበሩትን የበደሉትንና ያልበደሉትን ሁሉ ገዛቸው፡፡ ታላቁ ሙሴ እንኳን ሌላውን ሲያድን ራሳቸውንም ከሞት ማዳን ስላልተቻላቸው ለሞት ተገዝተዋል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር የጸጋው ስጦታ በኃጢአታችን ልክ የተደረገብን አይደለም፡፡ ራሱን ቤዛ አድርጎ ካሰልን፤ ከዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠን ጸጋ በጥምቀት፣ በሃብት፣ በልጅነት ለሰው ሁሉ ሕይወት በዛለት፡፡ ሮሜ ፭፥፲፮‐፲፰ የተነሣውን ክርስቶስን ሐዋርያት አይተውታል ገጽ በገጽ ዓይን በዓይን ፊት ለፊት ተያይተዋል፡፡ ሰግደውለታል፤ አመስግነውታል፤ ደስታቸው ፍጹም ሆኖላቸዋል፡፡ “… እናንተ አሁን ታዝናላችሁ ነገር ግን እንደ ገና አያችኋለሁ ልባችሁም ደስ ይለዋል ደስታችሁንም የሚወስድባችሁ የለም” ያለው የተፈጽሞላቸዋል፡፡ ዮሐ ፲፮፥፳፪ ለትምህርታቸው መሠረት ለስብከታቸው መነሻ የሆነው የጌታ ትንሣኤ ነው ምስክርነታቸውም የጸናው በትንሣኤ ነው፡፡ የተልእኳቸው ዋነኛ ዓላማ ሞቱንና ትንሣኤውን በመመስከር ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ሐዋ ፩፥፳፣ ሐዋ ፪፡፴፪፣ ሐዋ ፬፡፳
ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ በተለያዩ ቦታዎችና ጊዜያት እየተገለጠ ታይቶአል፡፡ እስከዓረገበት ዓረባኛው ቀን ድረስ ከሐዋርያት ብዙ አልተለየም፡ ከዚህም ሁሉ ጋር በሐዋርያት ትምህርትና ሥርዓተ ጸሎት አካባቢ የነበሩ ሳይቀሩ ብዙዎች አይተውታል፡፡ ከሁሉም በቀዳሚነት ማርያም መግደላዊት ዮሐ ፳፥፲፬‐፲፰ በመቃብሩ አካባቢ ነበሩ እነማርያም ባውፍልያ ማቴ ፳፰፥፱ ወደ ኤማሁስ ይጓዙ የነበሩ ሁለት ደቀመዛሙርት ሉቃ ፳፬፥፲፫‐፴፩ ስምኦን ጴጥሮስ ሉቃ ፳፬፥፴፬፣፩ቆሮ ፲፭፥፭ አሥሩ ደቀመዛሙርት ዮሐ ፳፥፲፱ አሥራ አንዱ ሐዋርት ዮሐ ፳፥፳፮ ከዳግም ትንሣኤ /ከሁለተኛው ሰንበት/ በኋላ ሰባቱ ደቀመዛሙርት ዮሐ፳፩፥፩‐፳፪ በገሊላ አሥራ አንዱ ሐዋርት ማቴ ፳፰፥፲፮ ማትያስ ባለበት አሥራ አንዱ ፩ቆሮ ፲፭፥፭ ሐዋ ፩፳፥፮ ከአምስት ጀምሮ (፭፻) የሚበዙ ወንድሞች ፩ቆሮ ፲፭፥፯ሐዋርያው ያዕቆብ ፩ቆሮ ፲፭፥፯-፲፪ ሁሉም ሐዋርያት በየጊዜውና በየቦታው አይተውታል፡፡ ማር ፲፮፥፲፱፣ ሉቃ ፳፬፥፶፣ ሐዋ ፩፥፫‐፲፪፣ ቁ ፳፮ በመጨረሻም ለቅዱስ ጳውሎስ ተገልጦለታል፡፡ ፩ ቆሮ ፲፭፥፰ 

እንግዲህ ክርስቶስን የምናገኝው እሱን በማመን ጸንተን፤ በፍቅሩ መስለነው በፈለገነው መጠን ስለሆነ፤ በፍጹም ፍቅሩ በሰጠን የልጅነት ጸጋ የክብሩ ወራሾች ለመሆን እንድንበቃ የትንሣኤውን ብርሃን በየልባችን ይሳልብን! አሜን፡፡

LIKE OUR PAGE >>>

Friday, April 11, 2014

መጋቢት 22

መጋቢት 22 ጥንተ ሆሳዕና ፤ ጌታችን መድሐኒታችን እየሱስ ክርስቶስ በአህያና በአህያይቱ ውርንጫ ተቀምጦ ወደ እየሩሳሌም የገባበት ከሁለት ሺ ዓመት ገደማ በፊት ልክ በዛሬዋ ቀን ነው። ጥንተ ሆሳዕና የሚባለውም ለዚያ ነው፤ ነገር ግን በዲሜጥሮስ ቀመር መሰረት ሆሳዕና እሁድን ሳይለቅ ከትንሳኤ አንድ ሳምንት ቀድሞ እንዲከበር ቤተክርስቲያን ስርዓት ብትሰራም ቅሉ መጋቢት 22 ይህንን ቀን ''ጥንተ ሆሳዕና" ብላ አስባው ትውላለች። በዛሬው ቀን የሚነበቡት ምንባባት በሙሉ ሆሳዕናን የሚመለከቱ ናቸው፤ ቅዳሴውም ቅዳሴ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ ቅዳሴ ውስጥ ስለ ሆሳዕና በስፋት ይናገራልና፤ ምስባኩም መዝ 8፤2 " ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ" የሚነበበው ወንጌልም ከአራቱ ወንጌላውያን የአንዱ ሆሳዕናን የሚመለከተ ነው፤ ማቴ 21፤4። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

LIKE OUR PAGE >>>

መጋቢት 20

በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት ጽጌ ሥላሴ አረፈች ባህታዊት ጽጌም ይሏታል፤ ስንክሳሩ ይጠቅሳታል ። የትውልድ ቦታዋ ሸዋ ተጉለት ነው፤ ወላጆቿ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፤ መንፈሳዊ ትምህርት እንድትማር ለገዳሙ መምህር ሰጧት እርሷም ከትምህርቷ ባሻገር መምህሯ ሲሰግድ ሲጸልይ እየተመለከተች አደገች፤ ስርዓተ ሃይማኖትን፤ ገዳመ መነኮሳትን፤ቀኖና መጽሐፍት፤ትርጓሜውን ሁሉ ጠንቅቃ አወቀች፤ በጾም በጸሎት የምትጋደልም ሆነች፤ መናፍቃንን ተከራክራ ትረታ ነበር፤ የዚህች ቅድስት እናት ታቦቷ ጥንት በአቡነ ሐራን ድንግል ገዳም ይግኝ እንደነበረ አሁን ግን ያለበት እንደማይታወቅ ሊቀ ብርሃናት መርቆሪዎስ አረጋ ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን በሚል መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል፡፡ ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ አቡነ ሐራ ድንግል እረፍታቸው ጥር 11 ቀን ነው፤ አስገራሚ ገዳማቸው በደቡብ ጎንደር ይገኛል ስጋቸው ከተቀበረበት ቦታ በየቀኑ እምነት ይፍልቃል የህን እምነት በቁና ዝቀው ይወስዱታል ጠዋት ሲመለሱ ድጋሚ ሞልቶ ያገኙታል፤የሚገርም ነው፤ ይህ የነበረ ሳይሆን አሁንም ያለ ታአምር ነው፤ ህሙማን ይህን እምነት እየተቀቡ ይፈወሳሉ ጸበሉንም እየተጠመቁ ይድናሉ፤ ሄዶ መመልከት ነው። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን የተመሰገነች የከበረች ተጋዳይም የሆነች አስጠራጦኒቃ በሰማዕትነት አረፈች፤ አባቷ ጣኦት አምላኪ ነው እርሷ ግን በክብር ባለቤት በክርስቶስ የምታምን ናት ስጋዋ እስቲከሳና እስክትደርቅ መልኳም እስቲለወጥ ድረስ በስውር ትጾም ትጸልይ ነበር፤ ከእለታት በአንዱ ቀን ወላጆቿ “እህል ከቤታችን አልጠፋም ለመሆኑ እንደዚህ የሚያከሳሽ ምንድን ነው” አሏት እርሷም “እኔስ ስለኃጢያቴ ወደ ክርስቶስ እጸልያለው” አለቻቸው፤ የክርስቶስን ስም ስትጠራ አባቷ ተቆጣ፤ ለጢባርዮስም አሳልፎ ሰጣት፤ “እናትና አባቴ ተውኝ እግዚያብሔር ግን ተቀበለኝ” አይደል ያለው ዳዊት ፤ በብዙ አሰቃያት በዛሬዋ ቀንም አንገቷን ቆርጠው ገደሏት፤እርሷም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች፤ የዚህችን እናት ጽናት ያዩ ብዙ አረማውያን በክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ሞተዋል። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን

LIKE OUR PAGE >>>

ኒቆዲሞስ



የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሰንበትና ሳምንቱ ኒቆዲሞስ ይባላል። ኒቆዲሞስ የተባለበትም ምክንያት በዚሁ ሰንበት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ከዋዜማው ጀምሮ «ወሀሎ አሐዱ ብእሲ እምፈሪሳውያን ዘስሙ ኒቆዲሞስ መልአኮሙ ለአይሁድ ዞሖረ ኃቤሁ ቀዲሙ ሌሊተ ወይቤሎ ለኢየሱስ ዕጓለ አንበሳ ሰከብከ ወኖምከ አንሥአኒ በትንሣኤከ፡- ስሙ ኒቆዲሞስ የሚባል የአይሁድ አለቃ የሆነ ከፈሪሳውያን ወገን አንድ ሰው ነበረ፡፡ እሱ አስቀድሞ ሌሊት ሄዶ ኢየሱስን በመቃብር አንቀላፋህ በትንሣኤህ አንሣኝ» ያለው ነው፡፡
ኒቆዲሞስ ሰገደ መንፈቀ ሌሊት ለዘቀደሳ ለሰንበት፡- ሰንበትን ለአከበራት ጌታ ኒቆዲሞስ ኢየሱስን ረቢ አብ መምህር ሆነህ ከአብ ዘንድእንደመጣህ እናምንብሃለን አለው፡፡» እያለ ኒቆዲሞስ ሌሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ እየሔደ ይሰግድ እንደነበረና ምሥጢረ ጥምቀትን ከእሱእንደተማረ እየጠቃቀሰ እያነሣሣ ስለሚዘምር ይህ ሰንበት ለዚሁ ጌታችን ኢየሱ
ስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስ ከጌታ ለመማሩ መታሰቢያ ሆኖ ስለተሰጠነው፡ የዚህ በዓል ታሪክ ዝርዝር ሁኔታው በዮሐንስ ወንጌል ምዕ 3 ቁጥ 1 እስከ 21 ተጽፏል፡፡
በዚህ ክፍለ ወንጌል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ምሥጢረ ጥምቀትን ብቻ ሳይሆን ርደቱን፣ ስቅለቱን፣ አዳኝነቱን አስተምሮታል፡፡ኒቆዲሞስ ከአርማትያሱ ከዮሴፍ ጋር ሆኖ ጌታን የገነዘው ታላቅ ሰው ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ሰንበት ከዚህ ጀምሮ የኒቆዲሞስ መታሰቢያ እስከ 3 ቀንይከበራል ማለት ማክሰኞ ድረስ የኒቆዲሞስ ቀኖች ናቸው፡፡
ሮሜ 7፡1-19
«ወንድሞች ሆይ ሕግን ለሚያውቁ እናገራለሁና ሰው ባለበት ዘመን ሁሉ ሕግ እንዲገዛው አታውቁምን) ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖርከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፤ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባል ከሆነው ሕግ ተፈትታለች፡፡ ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትሆንአመንዝራ ትባላለች፤ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትሆን አመንዝራ አይደለችም፡፡
እንዲሁ ወንድሞቼ ሆይ እናንተ ደግሞ በክርስቶስ ሥጋ ለሕግ ተገድላችኋል ለእግዚአብሔር ፍሬ እንድናፈራ እናንተ ለሌላው ከሙታን ለተነሣውለእርሱ ትሆኑ ዘንድ፡፡ በሥጋ ሳለን በሕግ የሚሆን የኃጢአት መሻት ለሞት ፍሬ ሊያፈራ በብልቶቻችን ይሠራ ነበርና፤ አሁን ግን ለእርሱለታሰርንበት ስለ ሞትን ከሕግ ተፈትተናል ስለዚህም በአዲሱ በመንፈስ ኑሮ እንገዛለን እንጂ በአሮጌው በፊደል ኑሮ አይደለም፡፡
እንግዲህ ምን እንላለን) ሕግ ኃጢአት ነውን) አይደለም፤ ነገር ግን በሕግ ባይሆን ኃጢአትን ባላወቅሁም ነበር፤ ሕጉ አትመኝ ባላለ ምኞትንባላወቅሁም ነበርና፡፡ ኃጢአት ግን ምክንያት አግኝቶ ምኞትን ሁሉ በትእዛዝ ሠራብኝ፤ ኃጢአት ያለ ሕግ ምውት ነውና፡፡ እኔም ዱሮ ያለሕግሕያው ነበርሁ፤ ትእዛዝ በመጣች ጊዜ ግን ኃጢአት ሕያው ሆነ እኔም ሞትሁ፤ ለሕይወትም የተሰጠችውን ትእዛዝ እርስዋን ለሞት ሆና አገኘኋት፤ኃጢአት ምክንያት አግኝቶ በትእዛዝ አታሎኛልና በእርስዋም ገድሎኛል፡፡ ስለዚህ ሕጉ ቅዱስ ነው ትእዛዚቱም ቅድስትና ጻድቅት በጎም ናት፡፡
እንግዲህ በጎ የሆነው ነገር ለእኔ ሞት ሆነብኝን) አይደለም ነገር ግን ኃጢአት ሆነ፤ ኃጢአትም በትእዛዝ ምክንያት ያለልክ ኃጢአተኛ ይሆን ዘንድኃጢአትም እንዲሆን ይገለጥ ዘንድ በጎ በሆነው ነገር ለእኔ ሞትን ይሠራ ነበር፡፡ ሕግ መንፈሳዊ እንደሆነ እናውቃለንና፤ እኔ ግን ከኃጢአት በታችልሆን የተሸጥሁ የሥጋ ነኝ፡፡ የማደርገውን አላውቅምና፤ የምጠላውን ያን የማደርገው አሁን እኔ አይደለሁም በእኔ የሚያድር ኃጢአት ነው፡፡እንጂ፡፡ በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፤ ፈቃድ አለኝና መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም የማልወደውን ክፉውን ነገርአደርጋለሁና ዳሩ ግን የምወደውን በጎውን ነገር አላደርገውም፡፡»
1 ዮሐ 4፡18
«ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል እንጂ በፍቅር ፍርሃት የለም ፍርሃት ቅጣት አለውና፤ የሚፈራም ሰው ፍቅሩ ፍጹም አይደለም፡፡ እርሱአስቀድሞ ወዶናልና እኛ እንወደዋለን፡፡ ማንም እግዚአብሔርን እወዳለሁ እያለ ወንድሙን ቢጠላ ሐሰተኛ ነው፤ ያየውን ወንድሙን የማይወድያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል) እግዚአብሔርንም የሚወድ ወንድሙን ደግሞ እንዲወድ ይህች ትእዛዝ ከእርሱ አለችን፡፡»
፡ሥራየሐዋ
«ነገር ግን በሕዝቡ ሁሉ ዘንድ የከበረ የሕግ መምህር ገማልያል የሚሉት አንድ ፈሪሳዊ በሸንጎ ተነሥቶ ሐዋርያትን ጥቂት ፈቀቅ እንዲያደርጉአቸውአዘዘ፡፡ እንዲህም አላቸው የእሥራኤል ሰዎች ሆይ ስለ እነዚህ ሰዎች ምን እንደምታደርጉ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፡፡ ከዚህ ወራት አስቀድሞ ቴዎዳስእኔ ታላቅ ነኝ ብሎ ተነሥቶ ነበርና አራት መቶ የሚያህሉ ሰዎችም ከእርሱ ጋር ተባበሩ፤ እርሱም ጠፋ የሰሙትም ሁሉ ተበተኑ እንደ ምናምንምሆኑ፡፡ ከዚህ በኋላ ሰዎች በተጻፉበት ዘመን የገሊላው ይሁዳ ተነሣ ብዙ ሰዎችንም አሸፍቶ አስከተለ፤ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ግን ታጠፉአቸውዘንድ አይቻላችሁም፤ በእርግጥ ከእግዚአብሔር ጋር ስትጣሉ ምናልባት እንዳትገኙ፡፡
ሰሙትም ሐዋርያትንም ወደ እነርሱ ጠርተው ገረፉአቸው፤ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው፡፡ እነርሱም ስለስሙ ይናቁ ዘንድየተገባቸው ሆነው ስለ ተቈጠሩ ከሸንጎው ፊት ደስ እያላቸው ወጡ፤ ዕለት ዕለትም በመቅደስና በቤታቸው ስለ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነማስተማርንና መስበክን አይተውም ነበር፡፡ »
፡መዝ
ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ
አመከርከኒ ወኢተረክበ ዓመጻ በላዕሌየ
ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው
ልቤን ፈተንኸው በሌሊትም ጐበኘኸኝ፡፡
ፈተንኸኝ ምንም አላገኘህብኝም፡፡
የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፡፡
፡ዮሐ
«ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ መምህር ሆይእግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔርዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን አለው፡፡ ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥትሊያይ አይችልም አለው፡፡ ኒቆዲሞስም፡- ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል) ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንደይችላልን) አለው፡፡ ኢየሱስም መለሰ እንዲህ ሲል፡- እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔርመንግሥት ሊገባ እይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው፡፡ ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላልሁህአታድንቅ፡፡ ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል ድምፁንም ትሰማለህ ነገር ግን ከወዴት እንደመጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም ከመንፈስ የተወለደሁሉ እንዲሁ ነው፡፡ ኒቆዲሞስም መልሶ ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል) አለው፡፡ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፡- አንተ የእሥራኤል መምህርስትሆን ይህን አታውቅምን) እውነት እውነት እልሃለሁ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን ምስክራችንንም አትቀበሉትም፡፡ስለምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ ስለሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ)»

ጐሥዓ ዘ እግዝእትነ ቅዳሴ

LIKE OUR PAGE >>>

Monday, March 31, 2014

ገብርሔር (ስድስተኛ ሳምንት)


ዛሬ ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛ ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተክርስቲያን «ገብርሔር» የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ገብርሔር በጎ አገልጋይ ማለት ሲሆን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ማቴ.25-14-30 ነው፡፡
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መሀከል አንዱ የሆነው ይህ የዛሬው ወንጌል አስተማሪ የሆኑ መሠረታዊ ጉዳዮችን በውስጡ ይዟል፡፡ በተለይ ምንም እንኳን የቤተክርስቲያን ሓላፊነት የእገሌና የእገሊት ተበሎ ባይወሰንም ቅሉ ቤተክርስቲያን ባላት የአገልግሎት መዋቅር መሠረት የሓላፊነትን ቦታ ይዘው ለሚያገለግሉ ሰዎች አትኩሮት ሊሰጡባቸው የሚገባቸውን ነጥቦች ይጠቁማል፡፡ ይህን ለማየት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና የሆኑ አሳቦችን በአትኩሮት መመርመር ጠቃሚ ነው፡፡

በምሳሌያዊው ታሪክ መጀመሪያ ላይ የምናገኘው አንድ መንገድ ሊጀምር ያሰበ ሰው ከመሔዱ በፊት አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው መጠን ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት እንዲሁም ለሌላኛው አንድ መክሊት ነግደው ያተርፉበት ዘንድ እንደሰጣቸው ነው፡፡

ገና ከታሪኩ መጀመሪያ እንደምንረዳው የአገልጋዮቹ ጌታ ምንም እንኳን እርሱ ለመንገድ ቢዘጋጅም ሀብቱ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ ተቆልፎበት እንዲቀመጥ አልፈለገም፡፡ በዚህም አገልጋዮቹን ጠርቶ ገንዘቡን በአደራ ተቀብለው «እንዲያተርፉበት» ማዘዙን እንደማስረጃ ልናቀርብ እንችላለን፡፡ ሆኖም ግን ማትረፍ በመፈለጉ ብቻ ገንዘቡን ያለአግባብ አልበተነም፡፡ ነገር ግን ለእርሱ ቀረቤታ የነበራቸውን አገልጋዮቹን ጠርቶ ያውም እንደየችሎታቸው መጠን ሓላፊነቱ ሳይከብዳቸው እንዲሠሩበት ገንዘቡን አከፋፈላቸው፡፡

ይህ ጌታ ቅንነትና ርኅራኄ የበዛለት እንደሆነ የሚያመላክተን ነገር አለ፡፡ ይኸውም ለአገልጋዮቹ ሓላፊነትን ቢሰጥም እንኳን ከእነርሱ ጋር በነበረው ቀረቤታ ማን ምን መሥራት ይችላል የሚለውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእያንዳንዳቸው እንደ ሓላፊነት የመሸከም አቅማቸው አምስት ሁለት አንድ እያደረገ መስጠቱ ነው፡፡

ምናልባት ስስት ባልተላቀቀው ስሜት ለሚያስብ ሰው የዚህ ጌታ መክሊት አሰጣጥ አድልዎ ያለበት ሊመስለው ይችላል፡፡ ታሪኩን እስከ መጨረሻው ብንከታተለው ግን የሚያሳየን የባለ መክሊቱን ባለቤት ቅንነት ነው፡፡ ቀጥለን እንደምናነበው ይህ ጌታ ለአገልጋዮቹ አትርፉበት ብሎ መክሊቱን ሰጥቷቸው በሔደበት ሀገር አልቀረም፡፡ ይልቁንም እያንዳንዱ በተሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩበት ሊቆጣጠራቸው እንደመጣ እናነባለን፡፡ ስለዚህ አገልጋዮቹ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩ እንደሚጠይቃቸው እያወቀ ከአቅማቸው በላይ የሆነ መክሊትን በመስጠት ምን ሠርተው የተሰጣቸውን መክሊት ያህል ማትረፍ እንደሚችሉ በማሰብ እንዲጨነቁ አልፈለገም፡፡ በተቃራኒው የምናየው ያለምንም ጭንቀት ከአእምሯቸው በላይ ሳይሆን ባላቸው ኃይል ተጠቅመው መሥራትና ማትረፍ የሚችሉትን ያህል መክሊት እንደሰጣቸው ነው፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩበት ሊቆጣጠራቸው ሲመጣ አምስት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ አምስት እንዲሁም ሁለት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ ሁለት መክሊት አትርፎ ጌታቸው ፊት እንደቆሙ ያ ጌታም በእነዚህ አገልጋዮቹ ታማኝነት ተደስቶ ወደ ደስታው እንዳስገባቸው እናያለን፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ያ አንድ መክሊት ተቀብሎ የነበረው ምድርን ቆፍሮ ያተርፍባት ዘንድ የተሰጠችውን መክሊት እንደቀበረ ከዚህም አልፎ ምን አደረክባት ተብሎ ሲጠየቅ የአመጽ ንግግር እንደተናገረ በዚህ ከፊቱ ያዘነው ጌታውም ያን ክፉ አገልጋይ እንዲቀጣ እንዳደረገው አናነባለን፡፡

በዚህኛው ክፍል ከተጠቀሰው ታሪክ ሦስቱን አካላት ማለት የመክሊቱን ሰጪ ጌታ፣ በጎ የተባሉ አገልጋዮችና ክፉ እና ሰነፍ የተባለውን አገልጋይ በተናጥል እንመልከታቸው፡፡

1. የአገልጋዮቹ ጌታ፡- 

ይህ ሰው ለገንዘቡ ጠንቃቃ ከመሆኑ ባሻገር በአገልጋዮቹ ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለው እናያለን፡፡ በክፉው አገልጋይ ላይ ባለመታዘዙ ምክንያት የፈረደበትን ፍርድ /ልቅሶና ጥርስ ማፏጨት ወዳለበት በውጪ ወዳለ ጨለማ አውጡት/ ስንመለከት የሚያሳየን የአገልጋዮቹን ጌታ ታላቅ ሥልጣን ነው፡፡ ምንም እንኳን ሥልጣኑ ጽኑ ቢሆንም ይህ ጌታ ፍርዱ ግን በእውነት ላይ የተመረኮዘ መሆኑን ደግሞ በድካማቸው ታግዘው በተሰጣቸው መክሊት ላተረፉት በጎ አገልጋዮች የሰጣቸውን ፍጹም ደስታ መጥቀስ ይቻላል፡፡

2. በጎ አገልጋዮች:-

በአገልጋዮቹ ጌታ በጎ አገልጋዮች የተባሉት አምስት መክሊት የተቀበለውና ሁለት መክሊት የተቀበለው ናቸው፡፡ እዚህ ጋር ማስተዋል የሚገባው እነዚህ ሁለቱ አገልጋዮች በጎ አገልጋዮች ለመባል ያበቃቸው አስቀድመው ብዙ ወይንም የተሻለ ቁጥር ያለው መክሊት ለመቀበል መብቃታቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ የመክሊቱ ቁጥር ሳይሆን በተሰጣቸው መክሊት መጠን የሚገባቸውን ያህል ደክመው ማትረፍ መቻላቸው ነው፡፡ ወይንም ያ ባለ አንድ መክሊት አገልጋይ ከሁለቱ ያሳነሰው ከአንድ በላይ መክሊት መቀበል የማይችል መሆኑ ሳይሆን በዚያችው በአንዷ መክሊት እንኳን መሥራት አለመቻሉ ነው፡፡

3. ክፉና ሰነፍ አገልጋይ:-

ይህ ሰው የተጠቀሱ ሦስት መሠረታዊ ችግሮች አሉበት፡፡
ሀ. የአገልጋዮቹ ጌታ ወደ መንገድ ሊሔድ በተዘጋጀበት ወቅት አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደችሎታቸው ገንዘቡን ሲሰጣቸው አትርፈው እንዲቆዩት ነው፡፡ ከላይ እንደተነገጋገርነው እንደ አቅማቸው መስጠቱም አቅማቸው በሚፈቅደው የሥራ ደረጃ እንዲሰማሩ በማሰብ ነበር፡፡ ይህ ሰነፍ አገልጋይ ግን ያደረገው ከታዘዘበት ዓላማ በተቃራኒው መልኩ ነው፡፡ ሊሠራበት የሚገባውን መክሊት ቀበረው፡፡ ይህም ለጌታው ትዕዛዝ ያለውን ቸልተኝነት ያሳያል፡፡

ለ. ጌታው በመጣ ጊዜ አመጽ የተመላበት የሐሰት ንግግር ተናግሯል፡- ከሔደበት ቦታ ተመልሶ ጌታው በተሰጠው መክሊት ምን እንዳደረገ ሲጠይቀው «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበሰብ ጨካኝ ሰው እንደ ሆንህ አውቃለሁ ስለፈራሁም ሔድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፡፡» ሲል መለሰለት፡፡ ይህ ንግግር ከአመጽ ንግግርነቱ በተጨማሪ ውሸት አለበት፡፡ ምክንያቱም እርሱ እንዳለው ጌታው ካልዘራበት የሚያጭድ ካልበተነበት የሚሰበሰብ ጨካኝ ሰው ቢሆን ኖሮ ያደርግ የነበረው ምንም መክሊት ሳይሰጠው ከነትርፉ ሁለት መክሊቶችን ይጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ተጽፎ የምናነበው ትርፉን ከመጠየቅ በፊት አንድ መክሊት ሰጥቶት እንደበረ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አስቀድሞ ገንዘቡን ዘርቶ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ጌታ ዘርቷልና ማጨድ ይገባዋል፤ በትኗልና መሰብሰብም መብቱ ነው፡፡

ሐ. እርሱ መሥራት ሲሳነው እንኳን ዕድሉን ለሌሎች አልሰጠም፡- ይህ ሰው የተሰጠው መክሊት በትርፍ ሊመለስ እንደሚገባው ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ገና ሲቀበል ከጌታው የተቀበለው ትዕዛዝ ነውና፡፡ ስለዚህ ምንም እንኳን መውጣት መውረዱ ቢከብደውም ወጥተው ወርደው ማትረፍ ለሚችሉ ሰዎች አለመስጠቱ ተጨማሪ ጥፋቱ ነው፡፡ ይህን እንዳያደርግ ያሰረው ደግሞ ውስጡ የተቀረጸው የአመጽ መንፈስ ነው፡፡ ጌታው መጥቶ ስለ ትርፉ ሲጠይቀው የሚመልስለትን ረብ የለሽ ምክንያት እንደ መከላከያ አድርጎ ማሰቡ አእምሮው ሌላ አማራጭ እንዳያስብ የዘጋበት ይመስላል፡፡

የመጽሐፈ ቅዱስ መተርጉማን አባቶች የዚህን ምሳሌያዊ ታሪክ ምስጢር ሲያስተምሩ የአገልጋዮቹ ጌታ የፍጡራን ጌታ የሆነ የእግዚአብሔር ምሳሌ እንደሆነ እንዲሁም ሦስቱ አገልጋዮች በተለያየ ደረጃ ያሉ ምዕመናንን እንደሚወክሉ ያስተምራሉ፡፡

ከዚህ የወንጌል ክፍል ምን እንማራለን?

ከተጠቀሰው ታሪክ የምንማራቸው ብዙ ነገሮች ቢኖሩም አበይት የሆኑትን ሁለቱን እንመልከታቸው፡፡

1. ለእያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር የተሰጠ ስጦታ እንዳለ እንረዳበታለን

እግዚአብሔር እያንዳንዳችን በሃይማኖት ሆነን የምናፈራውን ፍሬ ይፈልጋል፡፡ ምንም እንኳን ከእኛ ፍሬን ቢፈልግም ያን ፍሬ ማፍራት የምንችልበትን ኃይል ግን የእግዚአብሔርን ልጅነት ካገኘንበት ከዕለተ ጥምቀት ጀምሮ እንደሚያስፈልገን መጠን እየሰጠን ነው፡፡ 

ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበልናቸው ስጦታዎች በቁጥር እጅግ ብዙ ቢሆኑም በአይነታቸው ግን ለሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ዳግመኛ በመወለድ ምስጢር ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት ጸጋና ከልጅነት ጋር በተያያዘ የሚሰጡ ስጦታዎች ናቸው ፡፡ዮሐ.3-3 ሁለተኛው አይነት ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደ ሰውየው አቅም ለተለያዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች ማስፈፀሚያ ይሆኑ ዘንድ በእግዚአብሔር የሚሰጡ ስጦታዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ትንቢት መናገር ፣ በተለያዩ ልሳናት መናገር ፣ አጋንንትን ማስወጣት ... የመሳሰሉት ከዚህኛው አይነት ስጦታ የሚመደቡ ናቸው፡፡ 1ኛ ቆሮ.12-4፡፡ 

በመጀመሪያውም ይሁን በሁለተኛው አይነት ስጦታ ተቀባዮች ዘንድ ግን ብዙ የሚያሳዝኑ ችግሮች አሉ፡፡ በዳግመኛ መወለድ ምሥጢር (በ40 ና 80 ቀን ጥምቀት) ስላገኘነው የልጅነት ጸጋ ጊዜ ሰጥቶ የሚያስብ ክርስቲያን ማግኘት በዚህ ዘመን በጣም አዳጋች ነው፡፡ በዓመት ውስጥ ክርስቲያንነቱ ለጥምቀት በዓልና ለመስቀል ደመራ ካልሆነ ትዝ የማይለው ቁጥሩ ቀላል አይደለም፡፡ ከዚህ የከፋው ደግሞ ከቤተ ዘመድ አንድ ሰው ምናልባትም ራሱም ሊሆን ይችላል ነፍሱ ከሥጋው ካልተለየች ወደ ቤተ ክርስቲያን ደጅ ብቅ አይልም፡፡

እግዚአብሔር ለእኛ የልጅነትን ጸጋ በመስጠቱ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅሩን አሳይቶናል፡፡ ምክንያቱም ልጅነታችን ዋጋ ተከፍሎበታልና፡፡ እንዲሁ በቀላሉ አይደለም ልጆች የተባልነው፡፡ እኛ ልጅነትን እንድንቀበል አምላክ መከራን ተቀብሏል፡፡ የጥምቀታችን ውሃ የፈሰሰው በጦር ከተወጋው ከጌታ ጎን ነው ፡፡ ዮሐ.19-24፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይሄንን ሁሉ ሲያመለክት ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደሰጠን እዩ፡፡›› 1ኛ ዮሐ.3-1 ያለው፡፡

እኛ ልጆቹ እንሆን ዘንድ እግዚአብሔር ካሳየን የአባትነት ፍቅር በተጨማሪ ልጆቹ ስለመሆናችን የገባልንም ተስፋ ከአዕምሮ በላይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ምዕመናን በላከው መልእክቱ ‹‹እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፡፡ ልጆች ከሆናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፡፡›› ገላ.4-7 ስለሚጠብቀን ተስፋ ነግሮናል፡፡

ትልቁ ችግር ግን ተጠማቂው ሰው ይህን የልጅነት ክብር አለመረዳቱ ነው፡፡ የልጅነቴን ክብር ተረድቻለሁ እያለ የሚያወራውም ቢሆን የልጅነቱን መክሊት በልቡናው ውስጥ ቀብሮ አንድም ፍሬ ሳያፈራ ስለማንነቱ ለማውራት ቃላት ሲመርጥ ጊዜውን ያባክናል፡፡ አብዛኛው ግን የክርስትና እምነት ደጋፊ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊገለጥ የሚገባው እንደ ሀገር ልጅነታችን በምናሳየው የደጋፊነት /የቲፎዞነት/ ስሜት አይደለም፡፡ ደጋፊነት በጊዜ ና በቦታ ለተወሰነ ያውም ኃላፊ ለሆነ ድርጊት ነው፡፡ ክርስትና ግን በማንኛውም ቦታ፣ ጊዜ የሚኖርበት የህይወት መስመር እንጂ የሚደገፍ ጊዜያዊ ድርጊት አይደለም፡፡

ስለዚህ በጣም ልንጠነቀቅበት የሚገባን የመጀመሪያው መክሊታችን ልጅነታችን መሆኑን መረዳት ያስፈልገናል፡፡በዚህም መክሊት እንድንሰራ የታዘዝናቸውን ምግባራት እንድናፈራ የሚጠበቅብንን ፍሬዎች ማፍራት አለብን፡፡ ያለበለዚያ መክሊቱን እንደቀበረው ሰው መሆናችን ነው፡፡ 

2. እያንዳንዱ ስጦታ እንደሚያስጠይቅ እንረዳለን

እግዚአብሔር ያለ አንድ አላማ ለሰዎች ኃላፊነትን የሚያሰከትል ስጦታ አልሰጠም አይሰጥምም፡፡ ማንም ከእግዚአብሔር የተቀበለ ሰው የተሰጠው ስጦታ ለሆነ አላማ ነውና ጥያቄ አለበት፡፡ ጠያቂው ደግሞ የስጦታው ባለቤት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ 

መንጋውን እንዲጠብቁለት ሥልጣንና የተለያዩ የአገልግሎት ሰጦታዎችን እግዚአብሔር የሰጣቸው አሉ፡፡ዮሐ. 21-15 ፤ ገላ.1-15-16፡፡ ሆኖም ግን የተሰጣቸው ኃላፊነት የሚያስጨንቃቸው፣ ከልባቸው በእውነተኛ ትህትና የሚተጉ ያሉትን ያህል የሚያገለግሉበትን ስጦታ ከእግዚአብሔር መቀበላቸውን እንዲሁም የሚያስጠይቃቸው መሆኑን እስኪዘነጉ ድረስ መንገዳቸውን የሳቱ አሉ፡፡ በእግዚአብሔርና በሰዎች መሀከል እንደ ድልድይ ሆነው ያገለግሉበት ዘንድ በተሰጣቸው ሥልጣን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር የሚፈፅሙ ሰዎች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡

እንዲሁም ደግሞ ተሰባኪውን ወደ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ የነሱ ደጋፊ፣ ስለክብራቸው ተሟጋች እንዲሆን በህዝቡ መሀከል ጎራ እንዲፈጥርና የጳውሎስ ነኝ የአጵሎስ ነኝ እንዲል የሚያደርጉት ሰባኪዎችም ሌሎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ማንም ይሁን ማን ግን ስለተሰጠው መክሊት ባለቤቱ ከፊቱ አቁሞ እንደሚጠይቀው መዘንጋት የለበትም፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዲ/ን አባተ አስፋ


LIKE OUR PAGE >>>

Thursday, March 27, 2014

መጋቢት 19

በዚህች ቀን የብርሃናተ ዓለም የቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙር የሆነው ሐዋርያው አርስጣባሉ በሰማዕትነት አረፈ። ይህ ሐዋርያ ቁጥሩ ከ 72ቱ አርድእት ነው፤ በአምሳኛው ቀን ለሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ አብሮ ነበር፤ በኃላም ቅዱስ ጳውሎስን ተከትሎ አገር ለአገር እየዞረ ወንጌልን አስተማረ፤ ቅድስናውን በተመለከቱ ጊዜ አባቶቻችን ሐዋርያት አብራጣብያስ በሚባል አገር ኤጲስ ቆጶስ አድርገው ሾሙት እርሱም ወረደ ተወለደ ሞተ ተቀበረ ተነሳ ዳግም ለምጽአት ይመጣል፤ በእርሱ ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ይፈረድበታል እያለ ክርስቶስን ሰበከላቸው ብዙዎች አመኑ ተጠመቁም ቤተክርስቲያን አንጾላቸው ዲያቆን ካህን ሾሞላቸው ሲያበቃ ወንጌልን ለማስፋት ወደ ሌላ አገር ሄደ፤ በዚያም ሲሰብክ ሲያስተምር ዓላውያን ጣኦት አምላኪዎች ያዙት በብዙም አሰቃዩት በዛሬዋ ቀንም ገደሉት፤ እርሱም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ፤ ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ሰዎች መልእክትን ሲጽፍ የዚህን አባት ስም አንስቶ ሰላምታ አቅርቦለታል ሮሜ 16፤10። ከቅዱስ ገብርኤልና ከሐዋርያው አርሰጣባሉ በረከት ያሳትፈን። 

LIKE OUR PAGE >>>