Friday, April 11, 2014

መጋቢት 20

በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት ጽጌ ሥላሴ አረፈች ባህታዊት ጽጌም ይሏታል፤ ስንክሳሩ ይጠቅሳታል ። የትውልድ ቦታዋ ሸዋ ተጉለት ነው፤ ወላጆቿ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፤ መንፈሳዊ ትምህርት እንድትማር ለገዳሙ መምህር ሰጧት እርሷም ከትምህርቷ ባሻገር መምህሯ ሲሰግድ ሲጸልይ እየተመለከተች አደገች፤ ስርዓተ ሃይማኖትን፤ ገዳመ መነኮሳትን፤ቀኖና መጽሐፍት፤ትርጓሜውን ሁሉ ጠንቅቃ አወቀች፤ በጾም በጸሎት የምትጋደልም ሆነች፤ መናፍቃንን ተከራክራ ትረታ ነበር፤ የዚህች ቅድስት እናት ታቦቷ ጥንት በአቡነ ሐራን ድንግል ገዳም ይግኝ እንደነበረ አሁን ግን ያለበት እንደማይታወቅ ሊቀ ብርሃናት መርቆሪዎስ አረጋ ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን በሚል መጽሐፋቸው ጠቅሰውታል፡፡ ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ አቡነ ሐራ ድንግል እረፍታቸው ጥር 11 ቀን ነው፤ አስገራሚ ገዳማቸው በደቡብ ጎንደር ይገኛል ስጋቸው ከተቀበረበት ቦታ በየቀኑ እምነት ይፍልቃል የህን እምነት በቁና ዝቀው ይወስዱታል ጠዋት ሲመለሱ ድጋሚ ሞልቶ ያገኙታል፤የሚገርም ነው፤ ይህ የነበረ ሳይሆን አሁንም ያለ ታአምር ነው፤ ህሙማን ይህን እምነት እየተቀቡ ይፈወሳሉ ጸበሉንም እየተጠመቁ ይድናሉ፤ ሄዶ መመልከት ነው። ዳግመኛ በዛሬዋ ቀን የተመሰገነች የከበረች ተጋዳይም የሆነች አስጠራጦኒቃ በሰማዕትነት አረፈች፤ አባቷ ጣኦት አምላኪ ነው እርሷ ግን በክብር ባለቤት በክርስቶስ የምታምን ናት ስጋዋ እስቲከሳና እስክትደርቅ መልኳም እስቲለወጥ ድረስ በስውር ትጾም ትጸልይ ነበር፤ ከእለታት በአንዱ ቀን ወላጆቿ “እህል ከቤታችን አልጠፋም ለመሆኑ እንደዚህ የሚያከሳሽ ምንድን ነው” አሏት እርሷም “እኔስ ስለኃጢያቴ ወደ ክርስቶስ እጸልያለው” አለቻቸው፤ የክርስቶስን ስም ስትጠራ አባቷ ተቆጣ፤ ለጢባርዮስም አሳልፎ ሰጣት፤ “እናትና አባቴ ተውኝ እግዚያብሔር ግን ተቀበለኝ” አይደል ያለው ዳዊት ፤ በብዙ አሰቃያት በዛሬዋ ቀንም አንገቷን ቆርጠው ገደሏት፤እርሷም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች፤ የዚህችን እናት ጽናት ያዩ ብዙ አረማውያን በክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ሞተዋል። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን

LIKE OUR PAGE >>>

No comments:

Post a Comment